በቀጫጫ ደመወዝ ይሄን ሁሉ የኑሮ ቋጥኝ ተሸክመን የምንጓዝ አስማተኞች።
ከዚች ቀጫጫ ደመወዝ የቤት ኪራይ ከፍለንላት፣ የትራንስፖርት ከፍለንላት፣ የልጆች ትምህርት ቤት ወጪ ሸፍነንባት፣ ላለማስፎገር ብለን ለታናናሾቻችን ተበድረን የላክናትን ሳንቲም ተክተንባት፣ ምን ተርፎን ምን በልተንና ምን ለብሰን እየኖርን እንዳለን ለራሳችንም ያልገባን አስማተኞች!
የራሳችንን ስራ እንጀምር ብንል እንኳን እድሜያችንን ሰውተን ያካበትነው ካፒታል “እርካታ” ብቻ ነው። የእርካታ ማከፋፈያ እንክፈት?? እርካታ ትገዙናላችሁ?? እንግዲያውስ የትም የማታገኙትን ጣዕም የያዘ እርካታ አለን።
የሀሙስና የእሁድ ልዩነት፣የሌሊትና የቀን ድንበር እስኪጠፋብን ድረስ ያገለገልንበት እርካታ!
ለልጆቻችን፣ ለሚስት/ባሎቻችን፣ ለቤተሰቦቻችን መሰጠት የነበረበትን ጊዜ የተቀማንበት እርካታ!
እንደ ቀደምቶቻችን ሙክት ስቦ የመሄድ ወጉ ባይደርሰን እንኳን ባዶ እጃችንንም ለገና፣ ለፋሲካ፣ለአረፋ ለመውሊድ… እናት አባቶቻችን እየናፈቁን ስራ ቦታ የዋልን ያደርንበት እርካታ!
እድር፣ ልደት፣ ክርስትና፣ ሰርግ፣ ሰደቃ …ወ.ዘ.ተ ከሚባሉ ማህበራዊ ሁነቶች እንደ ደሴት የተገለልንበት እርካታ!
ትፈልጉታላችሁ ይሄን እርካታ??
Anteneh Shitaw(MPH)
