በኢትዮጵያ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ የመጣውን የኩላሊት ህመም ስርጭት ለመግታት እና የታካሚዎችን እንግልት ለማቃለል የሚያስችል የኩላሊት እጥበት (ዲያሌሲስ) ህክምና ማዕከል ለማቋቋም የሚያስችል የአዋጭነት ጥናት ተዘጋጅቶ መጠናቀቁን ተስፋ የኩላሊት ታካሚዎች ማህበር አስታወቀ።
ማህበሩ በቅርቡ ባካሄደው የ2018 ዓ.ም ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ እንደገለጸው፤ ሊቀረጽ የታሰበው የኩላሊት እጥበት ህክምና ማዕከል ሲገነባ 220 የአዋቂዎች እና 20 የህፃናት የዲያሌሲስ ማሽኖችን በውስጡ የሚያቅፍ ይሆናል።
የማህበሩ ፕሮጀክት ስራ አስኪያጅ በኃይሉ ኢረና እንደተናገሩት፤ የኩላሊት ህመም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱ በጥናት በመረጋገጡ አደጋውን ለመግታት ማዕከሉን ማቋቋም አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል።
የማዕከሉን ግንባታ በተመለከተም 70 በመቶ የሚሆነው ወጪ በባንክ ብድር፣ ቀሪው 30 በመቶ ደግሞ ከህብረተሰቡና አጋር አካላት በሚሰበሰብ ገቢ የሚሸፈን እንደሚሆን ጠቁመዋል።
በጊዜ ሂደትም ማዕከሉ የራሱን ሕንፃ የመገንባትና ህሙማኑ በቋሚነት የተሻለ የህክምና አገልግሎት የሚያገኙበትን ሁኔታ የማመቻቸት አላማ እንዳለው የገለጹት በኃይሉ፤ መንግስት ለግንባታው የሚሆን ቦታ በነፃ ይሰጠናል የሚል ትልቅ እምነት እንዳላቸው አብራርተዋል።
ሙሉ በሙሉ በኩላሊት ህሙማን የተቋቋመው ተስፋ የኩላሊት ታካሚዎች ማህበር፤ በዋናነት በሕክምና ወጪ፣ በኩላሊት እጥበት ሕክምና እና በሌሎች ተያያዥ የታካሚዎች ችግሮች ላይ ድጋፍ በማድረግ ብሎም የታካሚዎች ድምፅ በመሆን እየሰራ እንደሚገኝ ከድርጅቱ የደረሳት መረጃ ያመላክታል።
አሁን ላይ 230 የኩላሊት ታካሚ አባላት ያሉት ማህበሩ፤ ከህሙማኑ በሚሰበሰብ መጠነኛ መዋጮ፣ በለጋሾች፣ በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት በሚገኙ ኢትዮጵያውያን እንዲሁም 10 ብር ለኩላሊት እጥበት በሚል በጀመረው የገቢ ማግኛ ስልት አማካኝነት ከፍተኛ አቅም የሚጠይቀውን የኩላሊት እጥበት ወጪ ከግማሽ በላይ በመጋራት ሕክምናቸው እንዳይቋረጥ እያደረገ እንደሆነ አስታውቋል።
በዚህም በ2018 በጀት ዓመት 85 የማህበሩ አባላት የኩላሊት እጥበት የህክምና ወጪ በሳምንት ለአንድ ጊዜ 4,000.00 ብር (በወር ለአራት ጊዜ) በመክፈል ድጋፍ ማድረጉን ገልጿል።
የኩላሊት ህመም አሁን ላይ በእያንዳንዱ ቤት እየገባ በመሆኑ ህብረተሰቡ ተገቢውን ጥንቃቄ እንዲያደርግ አሳስበው፤ ማዕከሉ እውን ይሆን ዘንድ በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት የሚገኙ በጎ ፈቃደኞች ሁሉ ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።
በተጨማሪም ህብረተሰቡ 10 ብር ለኩላሊት እጥበት በተባለው የማህበሩ የገቢ ማሰባሰቢያ ጥሪ አማካኝነት በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና በዳሽን ባንክ 3136 አጭር የሂሳብ ቁጥሮች ከ10 ብር ጀምሮ ድጋፍ ማድረግ እንደሚችሉ ማህበሩ አታውቋል።
