ላለፉት 24 ዓመታት በስፖርት ጋዜጠኝነት ዘርፍ በትጋትና በታማኝነት ያገለገለው የሀትሪክ ስፖርት ኤክስኪዩቲቭ ኤዲተር የሆነው ጋዜጠኛ ይስሀቅ በላይ፣ በሙያው ላሳየው ከፍተኛ አስተዋጽኦ ዕውቅና እና የሽኝት ፕሮግራም በአሜሪካ ሊካሄድለት መሆኑ ታውቋል።
ጋዜጠኛ ይስሀቅ በላይ በፊፋ እና በዓለም አቀፉ አትሌቲክስ ቀጥተኛ ግብዣ በ2008 የቤጂንግ ኦሎምፒክ ዝግጅትን፣ በ2010 የደቡብ አፍሪካ፣ በ2022 በካታር እና በ2026 የፊፋ የአለም ዋንጫን በካናዳና በአሜሪካ፤ በ2011 በጀርመን እና በ2015 በካናዳ የፊፋ የአለም የሴቶች ዋንጫን ፣በ2013 የአፍሪካ ዋንጫን በደቡብ አፍሪካ፣ በ2017 በለንደን፣ በ2022 በአሜሪካ ኦሪገን፣በ2023 በሀንጋሪ ቡዳፔስት እና በ2025 በጃፓን ቶኪዮ በአራት የአለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ፣ ከዚህ በተጨማሪ የኦቷዋ ማራቶንን በካናዳ ኢትዮጵያን በተደጋጋሚ ወክሎ የተሳተፈ ሲሆን፣ በ”The Best FIFA Football Awards” በሴቶች ዘርፍ የዓለም የኮከብ ተጫዋቾች ምርጫ ላይም ለስምንት ዓመታት ሀገሩን በብቸኝነት ወክሎ ድምፁን ሰጥቷል።
ከዚህ በተጨማሪም አርሴናልን በመላው ዓለም ተወዳጅ እንዲሆን ያደረጉትን አርሴን ቬንገርና ሌሎች ታዋቂ የዓለም እግር ኳስ ባለታሪኮች ጋር በመገናኘት ለኢትዮጵያውያን ልዩ ቃለ መጠይቆችን አቅርቧል።
ይህን ረጅም እና ፍሬያማ የሙያ አገልግሎትን በማክበር፣ በአሜሪካ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የዕውቅናና የሽኝት ፕሮግራም አዘጋጅተውለታል።
ፕሮግራሙ ሐሙስ ጁላይ 16 ቀን 2026 በዋሽንግተን ዲሲ 4306 Georgia Ave NW,
Washington,DC 20011
ላሊበላ ሬስቶራንት የሚካሄድ ሲሆን፣ በሙያው ላይ ላሳየው ትጋት፣ ተጽዕኖ እና ለሀገሩ ላበረከተው አስተዋጽኦ የሚሰጥ የክብር መድረክ ይሆናል።
በአሁኑ ወቅትም የሀትሪክ ስፖርት ኦፊሺያሉ ጋዜጠኛ ይስሀቅ በላይ በኒውዮርክ ኒውጀርሲ የሚካሄደውን የፍጻሜ ጨዋታን በአካል በመገኘትና በመታደም ለኢትዮጵያውያን ትኪስ መረጃዎቹንና የፍፃሜውን ድባብ ከቦታው ለማድረስ የፊፋን የመጰረሻ አፕሩቫል በመጠባበቅ ላይ ይገኛል።
ይህ የዕውቅና ፕሮግራም የአንድ ጋዜጠኛ የረጅም ዘመን ትጋት፣ ሙያዊ ታማኝነት እና ለሀገሩ ያበረከተውን አስተዋጽኦ የሚያከብር ልዩ አጋጣሚ በመሆኑ የሃሳቡ ባለቤቶች ክብር ይገባቸዋል።
