የ2018 ዓ.ም የግንቦት ወር አጠቃላይ የዋጋ ግሽበት መጠን 13.4 በመቶ ሆኖ መመዝገቡን የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት አስታውቋል።
ይህም በሚያዝያ ወር 2018 ዓ.ም ከነበረው 11.7 በመቶ ጋር ሲነፃፀር የ1.7 በመቶ ከፍተኛ ጭማሪ ያሳየ ሲሆን፣ ባለፉት ጥቂት ወራት በሀገሪቱ እየታየ ያለዉ የዋጋ ንረት በግንቦት ወር ላይም በስፋት የተስተዋለ ሲሆን በዋናነት ደግሞ በምግብ ሸቀጦች ላይ የታየዉ ጭማሪ መሆኑን ተቋሙ ካፒታል ከተቋሙ ሪፖርት ተመልክቷል።
በወሩ የምግብና አልኮል ያልሆኑ መጠጦች ዋጋ ግሽበት 14.6 በመቶ የጨመረ ሲሆን፣ ለዚህም ዋነኛ መንስኤ የሆነው በዕለት ተዕለት የህዝብ ፍጆታ ውስጥ ከፍተኛ ድርሻ ያላቸው እንደ አትክልት፣ ስጋ፣ የወተት ተዋፅኦዎች፣ እንቁላል፣ ፍራፍሬ፣ የምግብ ዘይትና ስኳር የመሳሰሉት መሰረታዊ የምግብ ሸቀጦች ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ መጨመራቸው እንደሆነ መረጃው ያስረዳል።
በሌላ በኩል ምግብ ነክ ያልሆኑ የዋጋ ግሽበት መጠን በግንቦት ወር 11.1 በመቶ የደረሰ ሲሆን፣ በዚህ ዘርፍ ስር የሚገኙ ልዩ ልዩ የአገልግሎትና የዕቃዎች ክፍሎችም ከፍተኛ ጭማሪ አሳይተዋል።
በዚህም መሠረት ሌሎች እቃዎችና አገልግሎቶች 17.9 በመቶ፣ አልኮል መጠጦችና ትምባሆ 14.6 በመቶ፣ ትራንሰፖርት 12.1 በመቶ፣ ምግብ ቤቶችና ሆቴሎች 10.5 በመቶ እንዲሁም ኮሙዩኒኬሽን 9.1 በመቶ ሆነው መመዝገባቸው ታውቋል።
