በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል፤ በጋርዱላ ዞን ደራሼ ወረዳ ከመጋቢት 22 ቀን 2017 ዓ/ም ጀምሮ በተቀሰቀሰ ግጭት የሰዎች ሕይወት መጥፋቱና በርካታ ቤቶች መቃጠላቸዉን የአከባቢውን ነዋሪዎች ለቲክቫህ ኢትዮጵያ መናግራቸው ይታወሳል።
በወረዳዉ የሀይ’በረና እና ኦኖታ አከባቢ ነዋሪዎች ዛሬ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ እንደገለፁት ግጭቱ የመከላከያ ሰራዊት ወደ አከባቢው በመግባቱ መቆሙን ተናግረዋል።
በግጭቱ ምክንያት ሕይወታቸዉን ያጡትን የመቅበርና ሕዝቡን የማረጋጋት ስራ እየተሰራ መዋሉንም ገልጸዋል።
” የሞተዉ ሰዉ ቁጥር በጣም ብዙ ነዉ አስከሬናቸው እየተፈለገ ያሉም አሉ ” ያለን አንድ የአከባቢው ነዋሪ ” የተቃጠለዉ ቤት ብዛት ከቁጥር በላይ ነዉ ” ሲሉ ሁኔታዉን አብራርተዋል።
” የኛ ሁለት አጎቶች እስካሁን የገቡበት አልታወቀም፣ ልክ ግጭቱ እንደቆመ ቤተሰብ እያፈላለግን ነዉ ” ያለን ሌላኛዉ አስተያየት ሰጪ ” አሁን እየመሸ ስለሆነ የምናገኝ አይመስለንም፣ ሞተዉ ይሁን በህይወት ያሉ ፈጣሪ ነዉ የሚያዉቀዉ ” ብለዋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ የነዋሪዎችን ሃሳብ ተከትሎ በድጋሚ ወደ ጋርዱላ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ብርሃኑ ኩናሎ ደዉሎ የነበረ ሲሆን ሕዝብ እያወያዩ ብቻ እንደሆነ በመግለፅ ከዚህ ያለፈ መረጃ ለመስጠት እንደማይችሉ ገልፀዋል።
ከቲክቫህ ኢትዮጵያ
ሀዋሳ
