በግማሽ ዓመቱ ከ1መቶ36 ሺህ ዩኒት ደም በላይ መሰብሰብ መቻሉን የኢትዮጵያ ደምና ህብረ ህዋስ ባንክ ገለፀ።
።
የኢትዮጵያ ደም እና ህብረ ህዋስ ባንክ አገልግሎት በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ ስድስት ወራት በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ1መቶ36 ሺህ ዩኒት በላይ ደም መሰብሰቡን አስታውቋል።
የአገልግሎቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ሀብታሙ ታዬ እንደገለጹት፥ ተቋሙ በስድስት ወራት ውስጥ 1መቶ55 ሺህ ዩኒት ደም ለመሰብሰብ አቅዶ የዕቅዱን 84 በመቶ በማሳካት 1መቶ36 ሺህ ዩኒት ደም መሰብሰቡን ተናግረዋል።
ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ፥ ምንም እንኳን በአንዳንድ አካባቢዎች የነበረው የፀጥታ ችግር ፈተና ቢሆንም አፈጻጸሙ ግን አበረታች ነበር ብለዋል።
በተለይም በፀጥታ ችግር ውስጥ በነበሩት በአማራ ክልል እንደ ባሕር ዳር፣ ጎንደር፣ ደሴ እና ደብረ ማርቆስ ያሉ የደም ባንኮች ከዕቅዳቸው በላይ በመፈጸም አኩሪ ውጤት አስመዝግበዋል ነው ያሉት።
በኦሮሚያ ክልል እንዲሁም በአዲስ አበባ ከተማም የደም ልገሳ አፈጻጸሙ ከ90 በመቶ በላይ መሆኑን አስረድተዋል።፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ መጪውን የጥምቀት በዓል ተከትሎ የትምህርት ቤቶች መዘጋት እና በዓላት መደራረብ የደም እጥረት እንዳይፈጥር ተቋሙ ስጋት መኖሩን ገልጿል።
የደም እጥረት እንዳያጋጥምም ቅድመ ዝግጅት እያደረግን ነው ያሉት አቶ ሀብታሙ፥ የፊታችን ጥር 9 በአዲስ አበባ በሚገኙ ሁሉም አደባባዮች መጠነ ሰፊ የደም ልገሳ ዘመቻ እንደሚካሄድ ጠቁመው ህብረተሰቡ በንቃት እንዲሳተፍ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
