የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶችን በጎበኙበት ወቅት የ200 ቢሊዮን ዶላር የንግድ ስምምነቶች ይፋ ማድረጋቸው ይታወሳል።
ከእነዚህ ስምምነቶች መካከል ሁለቱ ሀገራት በሰው ሰራሽ አስተውሎት አብሮ መስራት የሚያስችላቸውን ስምምነት መፈጸማቸው ተነግሯል።
የአሜሪካ የንግድ ዲፓርትመንት እንደገለፀው፤ አሜሪካ እና የተባበሩት ዓረብ ኢምሬትስ “ዩኤስ-ዩኤኢ አክስለሬሽን ፓርትነርሺፕ” የተባለ ልዩ አጋርነት ለመፍጠር ተስማምተዋል። ይህ አጋርነት ሀገራቱ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዙሪያ ተቀራርበው እንዲሰሩ ያግዛል ተብሏል።
ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና የተባበሩት ዓረብ ኤሚሬቶች ፕሬዚዳንት ሼክ መሃመድ ቢን ዛይድ በአቡ ዳቢ የሚገኘው አዲሱ ባለ 5-ጊጋዋት የሰው ሰራሽ አስተውሎት ማዕከል ምዕራፍ አንድ መክፈቻ ላይ ተገኝተዋል።
ይህ አዲስ ባለ 5-ጊጋዋት የሰው ሰራሽ አስተውሎት ማዕከል ሲጠናቀቅ ከአሜሪካ ውጭ የሚገኝ በዓለም ላይ ትልቁ የሰው ሰራሽ አስተውሎት መገልገያ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል።
