ኮንፍረንስ አስመልክቶ በጦር መሳሪያ አንድን አገልጋይ ማጀብ እንደ ወንጌል አማኝ በፍፁም ተቀባይነት የሌለው ከአስተምሮት ውጪ መሆኑን የኢትዮጵያ ወንጌል አማኞች ቤተ ክርስቲያን ካውንስል አስታወቀ።
የካውንስሉ ፅ/ቤት ኃላፊ የሆኑት ፓስተር
ጌትነት ለማ በሰጡት መግለጫ የመንግስት አካላት ለአንድ አገልጋይ ፖሊስ አሰልፈው፣ መሳሪያ አስታጥቀው፣ አጀብ ፈጥረው ግርግር በማድረግ የሆነ አካል ወደ ከተማው የገባ የሚያስመስሉት ነገር ተገቢ እንዳልሆነ ተናግሯል።
እንደዚህ አጀብ ስላደረጋችሁ ለወንጌል አማኞች ክብር አይደለም፣ ብዙ አማኞች የመቃብር ስፍራ የላቸውም፣ የማምለኪያ ስፍራ የላቸውም እሱን አድርጉልን ብለዋል።
ጦሩ የመንግስት ነው፣ ሰራዊቱ የመንግስት ነው እጀባ አያስፈልግም ተብሏል። እንደዚህ በሚያደርጉ አገልጋዮች ላይ እርምጃ እንደሚወሰደ ካውንስሉ አስጠንቅቋል።
እጀባው ትርጉም አልባ ነው ከመፅሐፍ ቅዱስ ውጪ ነው በጦር መሳሪያ መታጀብ ትርጉሙ ሌላ ነው ፍርሃት ሲኖር ነው መታጀቡ የሚመጣው፣ አገልጋዩ ከህዝብ የተበደረው ገንዘብ ሲኖር ችግር የሚፈጥርብኝ ህዝብ ይኖራል ብሎ ሲፈራ ነው በፖሊስ የሚታጀበው እንጂ ወንጌል ለመስበክ ከሆነ እጀባ አያስፈልገውም ብለዋል።
በተደጋጋሚ እንደዚህ የሚያደርጉ አገልጋዮች በፅሁፍ፣ በአካል ማስጠንቀቂያ ሰጥተናል በቅርቡ እርምጃ ወስደን መግለጫ እንሰጣለን ብለዋል።
በተጨማሪም ዘይት የሚሸጡ አገልጋዮች ከመንግስት ንግድ ፍቃድ አውጥተው ሱቅ ከፍተው ዘይታቸውን መሸጥ ይችላሉ እንጂ በካውንስሉ ፍቃድ ዘይት የሚቸበችቡ ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ አስጠንቅቋል።
