በእስር ላይ የነበሩ የተቋማችን ሰራተኞች ምሽት ላይ ከተለቀቁ በኋላ ንብረቶቻችሁ ከማክሰኞ ሚያዚያ 14 ቀን 2017 ዓ.ም በኋላ ሊመለሱላችሁ ይችሉ ይሆናል ተብለናል።
ተቋማችን አዲስ ስታንዳርድ ሚዲያ በግልጽ ለህዝብ ማሳወቅ የሚፈልገው የተቋማችን ዋነኛ የዲጂታል መገልገያችን (main digital credentials) ምንም አይነት ጥቃት እንዳይደርስበት በአስተማማኝ ሁኔታ እንዲገኝ ያደረግን መሆኑን ነው።
ነገር ግን ከዚህ ውጭ ፖሊስ ባካሄደው ብርበራ በግዳጅ ከተወሰዱብን የኤሌክተሮኒክስ እቃዎች በተለይም ከስልኮቹ እና ኮምፒዩተሮቹ በተናጠል የሚላኩ ማናቸውም መልዕክቶች፣ ኢሜይሎች እንዲሁም ግንኙነቶች ተቋማችንን እንዲሁም ሰራተኞቻችንን የማይወክሉ መሆናቸውን ነው።
በተቋማችን ላይ ፖሊስ ብርበራ ካካሄደ በኋላ ባሉት ጊዜያት እነዚህ ኮምፒዩተሮች እና ስልኮች የሚገኙት በጸጥታ ሀይሎቹ እጅ ሲሆን በእነዚህ ኮምፒዩተሮች እና ስልኮች ምን እየተከናወነባቸው እንደሆነ የተረጋገጠ ነገር መግለጽ አንችልም።
ሆን ተብሎ በፋሲካ ዋዜማ እንዲህ አይነት ድርጊት በተቋማችን ላይ የተፈጸመው አፋጣኝ ምላሽ እንዳንሰጥ እና ሰራተኞቻችን ግራ እንዲጋቡ ለማድረግ መሆኑን መረዳት አያዳገትም።
በዚህ አጋጣሚ ህጋዊ እና ሰላማዊ የሆነ አካሄድን አሟጦ በመጠቀም የሰራተኞቻችን ደህንነት እና የኤሌክተሮኒክስ ንብረቶቻችንን ያለምንም ጥቃት መመለስ ለማረጋገጥ እንደምንሰራ ለማሳወቅ እንወዳለን።
በዚህ ፈታኝ ጊዜ የሚዲያ ተቋማችን ወዳጆች ሁኔታዎቹን እንድትረዱልን እያሳሰብን፣ ቀጣይነት ላለው ድጋፋችሁ ምስጋናችንን እናቀርባለን።
በየጊዜው የሚኖሩ ሁኔታዎችን እየተከታተልን እንደምናሳውቅ እንገልጻለን።
ፖሊስ የአዲስ ስታንዳርድ ጋዜጠኞችን ለእስር መዳረጉን እና የኤሌክትሮኒክስ ንብረቶችን መውሰዱን በተመለከተ የተሰጠ መግለጫ
Date:
