የአማራ ልማት ማኅበር (አልማ)፤ ለመቄዶንያ የአረጋዊያንና የአዕምሮ ሕሙማን ማዕከል ከ13 ሚሊዮን በላይ ብር የሚያወጡ የተለያዩ የሕክምና መሣሪያዎችን ዛሬ አስረክቧል።
የተደረገው ድጋፍ ወደ ማዕከሉ የሚመጡ ወገኖችን ጤና ከመጠበቅ ባሻገር በማዕከሉ የተጠለሉ ወገኖችን ሕይወትን የሚያሻሽል መኾኑን ተጠቃሚዎች ተናግረዋል።
ድጋፉ በሕክምና መሳሪያዎች እጥረት ይገጥማቸው የነበረውን ችግር በመፍታት በኩል ሚናው የላቀ መኾኑን በመቄዶንያ አረጋዊያንና አዕምሮ ሕሙማን ማዕከል የሚገኙ አረጋዊያን ገልጸዋል።
የመቄዶንያ ማኅበር መሥራች ቢኒያም በለጠ ተወካይ አቶ አሰፋ ባለሄር በበኩላቸው፤ አልማ ያደረገው የሕክምና ቁሳቁስ ድጋፍ የማዕከሉን የዕለት ተዕለት አገልግሎት አሰጣጥ የሚያሻሽል መኾኑን ገልጸዋል።
አልማ የዛሬውን ጨምሮ ከዚህ ቀደም የ17 ሚሊዮን ብር አልባሳትና ሌሎች ድጋፎችን በሦስት ዙሮች ማድረጉ ተገልጿል።
