የባህል መድኃኒት አዘጋጆች የሚያቀርቡትን ቅሬታ ለመመለስና በመመናመን ላይ ያሉ ሀገር በቀል እጽዋትን ቁጥር ለመጨመር፤ በተያዘው ዓመት ክረምት ለመድኃኒትነት የሚያገለግሉ 25 ሺሕ እጽዋትን ለመትከል ዝግጅት መጠናቀቁን ጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።
የጤና ሚኒስቴር ዴኤታ ወ/ሮ ፍሬህይወት አበበ፤ “በኢትዮጵያ ከሚገኙ እጽዋት መካከል በማኅበረሰቡ እና በመስኩ ባለሙያዎች ብቻ ሳይሆን ፈዋሽነታቸው በሳይንስ የተረጋገጠ የእጽዋት ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት ተጠናቋል” ብለዋል።
ሚኒስትር ዴኤታዋ በተጨማሪም፤ ለመድኃኒትነት የሚውሉ እጽዋትን ቁጥር ለመጨመር ከሚመለከታቸው የዘርፉ ባለሙያዎችና ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመሆን እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
በሽታው ከተከሰተ በኋላ ለማከም ጥቅም ላይ ከሚውሉት በተጨማሪ በሽታ ተከላካይ እንደሆኑ የሚታመንባቸው እጽዋትም ሊተከሉ ከተዘጋጁ እጽዋት መካከል ይገኙበታል ተብሏል።
በኢትዮጵያ ለመድኃትነት የሚወሉ በርካታ የእጽዋት ዝርያዎች ቢኖሩም፤ በበቂ ሁኔታ ተጠንተው ደረጃ ተሰጥቷቸዋል ማለት እንደማይቻል ወ/ሮ ፍሬህይወት አንስተው፤ “ችግኞችን ከመትከል ባሻገር መንከባከብ ላይም ትኩረት ማድረግ ይገባል” ብለዋል።
