አስመጪዎቹ እንደሚሉት፣ መስፈርቶቹ ተግባራዊ ሊሆኑ የማይችሉ ሲሆኑ፣ ብዙውን ጊዜ የአምራቾች ኃላፊነት የሆኑ መስፈርቶችን ከአስመጪዎች እንዲሟሉ መጠበቁ ንግዳቸውን አደጋ ላይ ሊጥለዉ እንደሚችል ስጋታቸውን ለካፒታል አቅርበዋል።
በአዲሱ መስፈርት ላይ ዋናው የአከራካሪ ጉዳይ ለተሽከርካሪዎች የተቀመጠዉ የባትሪ ደህንነት ማረጋገጫ ነዉ፣ ይህም አስመጪዎች የመኪና ተሽከርካሪ ባትሪዎች ዓለም አቀፍ የደህንነት መስፈርቶችን እንደሚያሟሉና እንዲያረጋግጡ ይጠይቃል።
አስመጪዎች ለካፒታል እንደተናገሩት “የባትሪ ደህንነት ማረጋገጫ ሊሰጥ የሚችለው አምራች እንጂ አስመጪ አይደለም” በማለት ይከራከራሉ።
የመኪናና የባትሪ አምራቾች ብዙውን ጊዜ የተለያዩ አካላት እንደሆኑ፣ አልፎ አልፎም በጋራ የሚሰሩ እንደሆነ አስረድተዋል። አስመጪዎች በአብዛኛው መኪናዎችን በብዛት ከሚያቀርቡ አቅራቢዎች ስለሚገዙ፣ ሚኒስቴሩ እንደሚጠይቀው በቀጥታ ከዋናው አምራች የባትሪ ደህንነት ማረጋገጫ ማግኘት “ለኢትዮጵያ አስመጪዎች የማይቻል” መሆኑን ገልጸዋል።
ሚኒስትሩ ፣ ሐምሌ 16 ቀን 2017 ዓ.ም. “ለሁሉም አሽከርካሪ አስመጪ ድርጅቶች በሚል ባወጣው ማስታወቂያ፣ እነዚህ አዳዲስ ደረጃዎች የተሽከርካሪ ማስመጫ ብቃት ማረጋገጫ ላይ የነበሩ የቀድሞ ችግሮችን ለመፍታት እንደተዘጋጁ አመልክቷል።
ማስታወቂያው ውጤታማ ከሆነበት ቀን ጀምሮ፣ ሁሉም በመካሄድ ላይ ያሉና የወደፊት የተሽከርካሪ ማስመጫ ብቃት ምዘናዎችና እድሳቶች በእነዚህ አዳዲስ መስፈርቶች መሰረት እንደሚሆኑ በግልጽ አስቀምጧል።
Source: capitalethiopia
