የሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን የአፍሪካ ቀንን አስመልክተው ለአፍሪካ ሕዝብ እና መሪዎች የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።
ፕሬዚዳንቱ የዘንድሮ የአፍሪካ ቀን ከሁለተኛ የዓለም ጦርነት ማብቃት እና ከተመድ ምሥረታ 80ኛ ዓመት፣ እንዲሁም ተመድ በቅኝ ግዛት ሥር ያሉ ሀገራት ነጻ እንዲሆኑ አዋጅ ያፀደቀበት 65ኛው ዓመት ጋር መገናኘቱ ታሪካዊ ያደርገዋል ብለዋል።
የናዚ መሸነፍ እና የቅኝ ግዛት ሥርዓት መወገድ የ20ኛው መቶ ክፍለ ወሳኝ ክስተቶች እንደነበሩ ያስታወሱት ፑቲን፣ ይህም ለሰው ልጅ ሁሉ ነጻ እና ሰላማዊ ኑሮ እጅግ አስፈላጊ እንደሆነ ገልጸዋል።
የአፍሪካ ሀገራት ነጻነታቸውን ባስከበሩባቸው ያለፉት ስድስት አሥርተ ዓመታት የዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ አካል ሆነው ማኅበረዊ እና ኢኮኖሚያዊ ስኬቶችን ማስመዝገባቸውንም ፕሬዚዳንቱ ጠቅሰዋል።
ፕሬዚዳንት ፑቲን በአፍሪካ ኅብረት ማዕቀፍ ውስጥ የተመሠረተው የባለ ብዙ ወገኖች ትብብር እንዲሁም በርካታ ቀጣናዊ ትብብሮች በአህጉሪቱ የፀጥታ እና መረጋጋት እንዲጠናከር አስተዋፅኦ አድርገዋል ብለዋል።
ሀገራቸው ከአፍሪካ ጋር የቆየውን የወዳጅነት ግንኙነት እንዲጠናከር እንደምትፈልግ ያወሱት ፑቲን፣ በ2019 እና በ2023 የተካሄዱት የሩሲያ-አፍሪካ ጉባኤዎች ሩሲያ እና አፍሪካ በዓለም አቀፍ ጉዳዮች ላይ የጋራ አቋም እንዲይዙ ማስቻላቸውን ገልጸዋል።
ፕሬዚዳንቱ በመጨረሻም ለአፍሪካ ሕዝብ ጤና፣ ስኬት፣ ሰላም እና ብልጽግናን ተመኝተዋል።
