*ለሱቅ የሚሆን ቤት ተሰጥቶታል
በኢትዮጵያ የኪነ- ጥበብ ታሪክ ውስጥ በዳይሬክተርነት እና በደራሲነት ያገለገለው ዳግማዊ አመለወርቅ ፈይሳ አድናቂዎቹ ፣የሙያ ጓደኞቹ በተገኙበት ለሱቅ የሚሆን ቤትና ሌሎች እስከ 3 ሚሊዮን ብር ስጦታ ተበርክቶለታል።
ሰኞ መጋቢት 7 2018 ከቀኑ 11ሰዓት በኃላ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር በተከናወነ ኪነ ጥበባዊ ዝግጅት የዳግማዊ ሥራዎች ተቀንጭበው የቀረቡ ሲሆን የሰርከስና የሙዚቃ መሰናዶዎችም ቀርበዋል።
ዳግማዊን በሊሞዚን ወደ ብሔራዊ ቴአትር በማምጣትም ኤልሻዳይ ዲኮር ሚናውን ተወጥቷል።
የምስጋና መርሀ ግብሩ አዘጋጅ ሔኖክ የእታገኝ ልጅ እንደሆነም ታውቋል። ሔኖክ፣ በፊልም ፕሮዳክሽኑ አማካይነት የምስጋና ዝግጅቱን ሀሣብ ከማመንጨት ጀምሮ እስከ ሁነቱ ፍፃሜ ድረስ ብዙ የለፋ ባለሙያ ነው።
“ስሙአተ ነገር” የሚል ርዕስ ባለው በዚህ መርሀ- ግብር ላይ ቴምር ሪል ስቴት የ3 ሚሊዬን ብር የሚያወጣ ለሱቅ የሚሆን ቤት በስጦታ መልክ ያበረከተለት ሲሆን በተጨማሪም የማስታወቂያ ባለሙያ ዘላለም ኩራባቸው መጠኑ ያልተገለፀ ገንዘብ ወደ ሙያ ላመጣው ታላቅ ሰው ለዳግማዊ አበርክቷል።
መስፍን አይፎክሩም በበኩሉ ለዳግማዊ ያለውን ፍቅር ለመግለፅ የወርቅ ሰዐት ሸልሞታል።
በመፅሐፍ ማሳተም የሚታወቀው ጃፋር መፅሐፍት መደብር በዕለቱ ለምረቃ የበቃውን በዳግማዊ አመለወርቅ ፈይሳ የተፃፈውን “ዝሀ” የሚል ርዕስ ያለውን መፅሐፍ አሳትሞለታል።መፅሐፉ 307 ገፆች ያሉት ሲሆን በ850 ብር የሚሸጥም እንደሆነ ታውቋል።
ይህንኑ መፅሐፍ ጠንክር ቴኒ የ100,000ብር ፣ ፍሬአለም ሺባባው የ50,000 ብር መፅሐፍ በመግዛት ለኪነ ጥበብ ባለሙያው ያላቸውን አክብሮት ገልፀዋል።
ዳግማዊ አመለወርቅ ፈይሳ በ1960 ዓ.ም አዲስ አበባ አብነት አካባቢ ጠጅ ሳር ሰፈር የተወለደ ባለሙያ ሲሆን ላለፉት 40 ዓመታት በኪነ ጥበቡ አለም የቆየ ነው።
ዳግማዋ ለ17 ዓመታት ያህል ስክሪፕት በመጻፍ ከ 500 በላይ ዶክመንተሪዎችንና 1000 ማስታወቂያዎችን በመስራት ድንቅ ባለሙያነቱንም አስመስክሯል።
ዓመል የቴሌቭዥን ድራማ፤ የቃቄ ውርዶዎት ከመጋረጃ ጀርባ የተሰኙ ቴአትሮችን ጨምሮ ከ40 በላይ በሚሆኑ የመድረክ ቴአትሮች ውስጥ በትወና በዝግጅትና በድርሰት ተሳትፏል፣በፊልሞች ላይም የራሱን ድንቅ አሻራ ያኖረው ዳግማዊ ዛሬም ለሙያው ያለውን መሰጠት በማሳየት ላይ ይገኛል።
የዕለቱን መርሀ ግብር በመደገፍ ኢትዮ ቴሌኮም፣ ቴምር ሪል ስቴትና ቢን ምዕራፍ የሚጠበቅባቸውን ድርሻ የተወጡ መሆኑ ታውቋል።
በሔኖክ የእታገኝ ልጅ አማካይነት ከዚህ ቀደም ለቴአትር ባለሙያዎች ተስፋዬ ሲማ እና ቢንያም ወርቁ ስሙአተ ነገር 1እና 2 በሚል ርዕስ የዕውቅና ዝግጅት ማድረጉ አይዘነጋም።
የዕውቅና መርሀ ግብሩ የተደረገለት ዳግማዊ አመለወርቅ ፈይሳ በተደረገለት ዕውቅና የደስታ ስሜቱን የገለፀ ሲሆን በህይወት ሳሉ መመሰጋገን ሊለመድ የሚገባ ባህል መሆኑንም ጨምሮ ገልጿል።
የዳግማዊ ፈይሣ የሙያ ታሪክ 6 ወር በፊት በወጣው መዝገበ አእምሮ ቅፅ 2 ኢንሳይክሎፒዲያ ላይ የተሰነደ ሲሆን አሳታሚው ዕዝራ እጅጉም የምስጋና መርሀ ግብሩ የሚድያ ማስተባበር ሥራንም ማከናወኑ ታውቋል።
