አውቶብሶችን፣ ባቡርንና ሌሎች የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎቶችን በስፋትና በአግባቡ መጠቀም፤ አገልግሎቱም በወጣለት ታሪፍና መርሃ-ግብር ያለ መቆራረጥ እንዲሰጥ ሚኒስቴር መ/ቤቱ ጠይቋል፡፡
የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስቴር “የኢትዮጵያን የትራንስፖርት ዘርፍ ወደ ኤሌክትሪክና የተፈጥሮ ጋዝ የማሸጋገር እና የነዳጅ ቁጠባ ሀገራዊ ጥሪ” በሚል ርዕስ መግለጫ አውጥቷል፡፡
በአሁኑ ወቅት በመካከለኛው ምስራቅ በተከሰተው ጦርነት ምክንያት የዓለም የነዳጅ ገበያ ከፍተኛ ጭማሪ እያሳየ ነው፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድም በትናትናው ዕለት ባወጡት መግለጫ ‘’ነዳጅን በቁጠባ እንጠቀም’’ ሲሉ ማሳሰቢያ ሰጥተዋል።
የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስቴርም ወቅታዊውን ዓለም አቀፍ ጫና ለመቋቋም እና የሀገርን ኢኮኖሚ በዘላቂነት ለመታደግ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል፣ በመንግስትና በግል ተቋማት ዘንድ ተግባራዊ እንዲደረጉ ብሎ ጥሪ ቀርቧል፡፡
በነዳጅና በኤሌክትሪክ የሚሰሩ (Plug-in Hybrid) ተሽከርካሪዎች ነዳጅን በመተው የኤሌክትሪክ ኃይልን ብቻ እንዲጠቀሙ ማስቻል፤ እንዲሁም በነዳጅ የሚሰሩትን ወደ ኤሌክትሪክና ተፈጥሮ ጋዝ የመቀየርስራን ማጠናከር፤ እስከ 20 ቶን የሚጭኑ የጭነት ተሽከርካሪዎች ወደ ኤሌክትሪክ፣ ከ20 ቶን በላይ የሆኑት ደግሞ ወደ ተፈጥሮ ጋዝና ኤሌክትሪክ እንዲቀየሩ መንግስትና የግሉ ዘርፍ በቅንጅት እንዲሰሩ መ/ቱ ጥሪ አቅርቧል፡፡
ከአንድ ቤት ውስጥ ብዙ መኪናዎችን ይዞ መንገድ ከመውጣት ይልቅ፣ በጋራ የመጠቀም ልምድን ማዳበርና ተግባራዊ ማድረግ፣በከተማ ውስጥ የሚደረጉ አጫጭር ጉዞዎችን በእግርና በብስክሌት የማድረግ ባህልን ማሳደግ ይገባል ሲልም ጥሪ አቅርቧል፡፡
የትብብር ጥሪው የሀገርን የውጭ ምንዛሬ ለማዳን፣ የአካባቢ ብክለትን ለመቀነስና ዜጎች በዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ መዋዠቅ እንዳይጎዱ ለማድረግ የታለመ ነው ሲልም የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስቴር ተናግሯል፡፡
