ሚያዝያ 30/2017 (አሐዱ ሬዲዮ) በአዋሽ ጉምሩክ ቅ/ጽ/ቤት በተደረገ ክትትል እና ፍተሻ መነሻውን መቀሌ ባደረገ በፈሳሽ ጭነት ማመላለሻ ተሽከርካሪ ታንከር ውስጥ በሕገ-ወጥ መንገድ ሲዘዋወር የነበረ 120 ሺሕ የአሜሪካን ዶላር በቁጥጥር ሥር መዋሉን የጉምሩክ ኮሚሽን አስታውቋል፡፡
ሕገ-ወጥ ዶላሩ በቁጥጥር ሥር የዋለው ምንም ፈሳሽ ጭነት ሳይጭን ወደ አዲስ አበባ መስመር እየተጓዘ በነበረ የፈሳሽ ጭነት ማመላለሻ ተሽከርካሪ ታንከር ውስጥ በፕላስቲክ እና በፕላስተር ተጠቅልሎ መሆኑም ተነግሯል፡፡
በዚህ ድርጊት የተሳተፉ ሁለት ተጠርጣሪዎችም በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ኮሚሽኑ ገልጿል፡፡
የኮንትሮባንድ እና ሕገወጥ ንግድ የአፈጻጸም ስልቱ ተለዋዋጭ በመሆኑ፤ ድርጊቱን ለመግታትና በሀገር ኢኮኖሚ የሚያሳድረውን ተጽእኖ ለመከላከል ሁሉም ባላድርሻ አካላትና ሕብረተሰቡ የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ የጉምሩክ ኮሚሽን ጥሪውን አቅርቧል፡፡
