የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፌደራል ገቢ ግብር አዋጅን ለማሻሻል የቀረበውን ረቂቅ አዋጅ አፅድቋል።
ረቂቅ አዋጁ በአብላጫ ድምጽ ነው የፀደቀው።
አዋጁ ሰፊ ክርክር ሲነሳበት እንደነበር ይታወቃል።
በተለይም የኢትዮጵያ ሰራተኛ ማሕበራት ኮንፌዴሬሽን (ኢሰማኮ) ረቂቅ አዋጁ ከመጽደቁ በፊት የደመወዝ ገቢ ግብር መነሻ ተብሎ የተቀመጠው 2,000 ብር ወደ 8,324 ብር ከፍ እንዲል ፤ አጠቃላይ አዋጁ የኑሮ ውድነቱንና ጫናውን ታሳቢ ባደረገ መልኩ እንዲታረም ሲወተውት ነበር።
የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ፤ ረቂቅ አዋጁን አስመልክቶ ያቀረበውን ሪፖርትና የውሳኔ ሃሳብ ከመረመረ በኋላ፣ አዋጁን አፅድቆታል።
ረቂቅ አዋጁ በተለይም በንግዱ ማህበረሰብና በተቀጣሪ ሠራተኞች ላይ ሊጣል የታሰበው የግብር ምጣኔ ከፍተኛ ነው የሚል ቅሬታ ሲነሳበት እንደቆየ ተዘግቧል፡፡
ከተለያዩ ወገኖች የቀረቡት አስተያየቶች፣ አሁን ካለው የኑሮ ውድነትና የዋጋ ንረት አኳያ፣ እስከ 35 በመቶ የሚደርሰው የገቢ ግብር መጠን መቀነስ እንዳለበት ይጠቁማሉ።
