በመቶዎች የሚቆጠሩ የዐይን ህመሞች እንዳሉ የህክምና ባለሙያዎች ይገልጻሉ፡፡ የዐይን ሞራ፣ ግላኮማ፣ የዐይን መንሸዋረር፣ የእንባ መውረጃ ቱቦ መዘጋት፣ የብርሃን መቀበያ መላቀቅ፣ የብሌን ጠባሳ፣ የዐይን ድርቀት እና የመነጽር ድጋፍ የሚሉት ከዐይን ህመሞች መካከል ጥቂቶቹ መሆናቸው ይጠቀሳል።
በዳግማዊ ምኒልክ ኮምፕርሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሪፈራል ሆስፒታል ከፍተኛ የዐይን ስፔሻሊስት ዶክተር ዮናስ አብርሃም እንደሚሉት፤ እርጅና እና ሲጋራ ማጨስ ለዐይን ህመም አጋላጭ ከሆኑ ምክንያቶች መካከል ናቸው።
በተጨማሪም ለብዙ ሰዓት ለአደገኛ የፀሐይ ጨረር መጋለጥ፣ ያልተመጠነ የስክሪን አጠቃቀም፣ በቤተሰብ ተወራራሽ የዐይን ችግርና አንዳንድ የሚወሰዱ መድኃኒቶች ለዐይን ህመም እንደሚያጋልጡ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ አብራርተዋል።
ከዐይን ህመም ምልክቶች መካከል፤ የዕይታ መቀነስ፣ አንድ ነገር ሁለት መስሎ መታየት፣ ማንፀባረቅ፣ መቅላት፣ ያለአግባብ ዕንባ ማንባት፣ የዐይን ውጋትና ቀለሞችን የመለየት አቅም መቀነስ እንደሚገኙበት ዘርዝረዋል።
የፀሐይና የስክሪን ጨረር የሚቀንስ መነጽር መጠቀም፣ የተመጣጠነ ምግብ (አትክልት፣ እንቁላል፣ ፍራፍሬ፣ ተልባ፣ ብሮኮሊ የመሳሰሉትን) መመገብ፣ ንጽህናን በአግባቡ መጠበቅ፣ የስክሪን አጠቃቀም ሰዓት መገደብ፣ ዓመታዊ የዐይን ምርመራ ማድረግ (በተለይ ለሕጻናትና ከ40 ዓመት በላይ ለሆኑ ሰዎች) መከላከያ መንገዶቹ መሆናቸውን ጠቅሰዋል።
በኢትዮጵያ በርካታ ሰዎች ለዐይን ህመም እንደሚጋለጡ የሚገልጹት የሕክምና ባለሙያው፤ መከላከያ ዘዴዎችን በአግባቡ መጠቀም እንደሚገባ መክረዋል።
ከዚህ አለፍ ያለ የዐይን ጤና እክል ከተከሰተ በሀገር ውስጥ በተለያዩ ሆስፒታሎች ሕክምናው እንደሚሰጥ በመግለጽ በወቅቱ ሐኪም ማማከር ተገቢ መሆኑን መግለጻቸውን ኢዜአ ዘግቧል።
