የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የግንባታ ፈቃድና ቁጥጥር ባለሥልጣን ከሀምሌ 5/2017 ዓ.ም ጀምሮ የግንባታ ቦታዎችን የሚመረምር አዲስ ግብረ-ሃይል ወደ ስራ እንደሚገባ ገልጿል።
በባለሥልጣን መስሪያ ቤቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር የሆኑት ኢንጂነር አበበ እሸቱ ይህ አዲስ ግብረ ኃይል በኮንስትራክሽን ቦታዎች ላይ በመንቀሳቀስ የሠራተኞችን ደኅንነት የማያስጠብቁ ወይም የደኅንነት ህጎችን የማያሟሉትን እንደሚለዩ ተናግረዋል።
ይህን ግብረ-ኃይል ማሰማራት ያስፈለገው እ.ኤ.አ ከ2022 ጀምሮ ደኅንነታቸው ባልተጠበቁ ቦታዎች ላይ ቢያንስ 142 ሠራተኞች መሞታቸውን ተከትሎ መሆኑን እና ይህ የሞት መጠን እያሻቀበ መሆኑን በተለያዩ ጊዜያት የሚፈጠሩ አደጋዎች በማመላከታቸው ነው ተብሏል።
በኮንስትራክሽን የሥራ ዘርፍ ከተሰማሩት ሠራተኞች ውስጥ 99 በመቶ የሚሆኑት መደበኛ የደኅንነት ሥልጠና እንደሌላቸው በጥናት ተገኝቷል።
ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ፥ “በከተማችን የግንባታ ስራዎች በሚካሄዱባቸው ቦታዎች ላይ በተደጋጋሚ የተለያዩ አደጋዎች ይከሰታሉ፣ ስጋቶችም አሉ። ለዚህ መንስኤው ሰራተኞች ስልጠና አለመውሰዳቸው እና ገንቢዎች ለሰራተኞች የሚሆኑ የደህንነት መጠበቂያ ግብአቶችን ባለማቅረባቸው ነው” ሲሉ ነው የገለጹት።
በግንባታ ቦታዎች ላይ በተለያዩ ምክንያቶች የሞቱ ሰራተኞች ቁጥር ይገለፅ እንጂ ተሸፋፍኖ የሚቀር ያልተቆጠሩ ሠራተኞች ስለመኖራቸውም ነው የተነገረው።
ባለስልጣን መስሪያ ቤቱም ከተለያዩ ክፍለ ከተማዎች ሠራተኞችን በመመደብ 2681 ግንባታዎችን መመልከት መቻሉን አንስቷል።
ከእነዚህ ውስጥም 1300 አካባቢ የሚሆኑት ብቻ ለሠራተኞቻቸው ሄልሜንት እና አንፀባራቂ ማሟላት የቻሉት። ይህ ማለት ከ50 በመቶ በላይ የሚሆኑት ህጎችን እያከበሩ አይደለም።
አብዛኞቹ ሠራተኞች አደጋ ላይ መሆናቸውን ተመልክተናል ያሉት ዳይሬክተሩ፥ የህንፃ ግንባታ ደኅንነት ያልጠበቀ ኮንተራክተር ወይም አልሚ የ50 ሺህ ብር ቅጣት እንደሚጣልበት በህግ ደረጃ ተቀምጧል ብለዋል።
አክለውም፥ አዲስ ግብረ ሀይሉ በሚለያቸው ግንባታዎች ቦታዎች ላይ እርምጃ ይወሰዳል ሲሉ ጠቁመዋል።
@TikvahethMagazine
