ለሠራተኞች የሙያ ስልጠና ሳይሰጥ ወደ ሥራ እንዲሰማሩ መደረጋቸው ለአደጋ ተጋላጭ እንዲሆኑ እያደረጋቸው እንደሚገኝ የኢትጵያ ሠራተኛ ማህበራት ኮንፌዴሬሽን አስታውቋል፡፡
በተለያዩ የሥራ መስኮች ላይ በተሰማሩ ሠራተኞች ስለ ሚሰሩት የሥራ መስክ በቂ የሆነ የሙያ ስልጠና እንዲሰጣቸው ማድረግ ከተቋማት የሚጠበቅ ኃላፊነት የሚጠበቅ መሆኑን የተናገሩት በኮንፌዴሪሽኑ የውጭ እና የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ ኃላፊ አያሌው አህመድ ናቸው፡፡
በተደጋጋሚ ሠራተኞች የተለያየ ጉዳት እየደረሰባቸው መሆኑን አንስተው፤ የሥራ ቦታቸው ከኬሚካል ጋር ግንኙነት ባላቸው ሠራተኞች ለጉዳቱ የበለጠ ተጋላጭ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
የሥራ የደህንነት መስፈርቶች ባለመሟላታቸው የሚደርሱ ጉዳቶች በዜጎችን ሕይወት ላይ ጫና እያሳደረ መሆኑን የገለጹት ኃላፊው፤ ሠራተኞች የሥራ ላይ ደህንነትን በተሟላ ሁኔታ ባለመከተላቸው ምክንያት ሕወታቸው እያለፈ እና ለአካል ጉዳት እየተዳረጉ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
በሥራ ቦታ ላይ ያለው የሥራ ደህንነት መስፈር በተመለከተ ክትትል የማያካሄድ ኃላፊነት ያለው የሥራ እና ክህሎት ሚኒስቴር ቢሆንም፤ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ችግሩን በብቸኝነት ሊፈታ ባለመቻሉ ሁሉም ባለ ድርሻ የበኩሉን ኃላፊነት ሊወጣ እንደሚገባ አሳስበዋል ።
