የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ከኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ጋር በመተባበር በዛሬው ዕለት “ከራዕይ ወደ ተግባር የኢትዮጵያ ዘላቂና አካታች የምግብ ስርዓት ሽግግር ጉዞ” በሚል መሪ ሀሳብ የፓናል ውይይት አድርጓል፡፡
በፓናል ውይይቱ የግብርና ባለሙያዎች፣ የዩኒቨርሲቲ ምሁራን፣ ጋዜጠኞች፣ የክልሎች ግብርና ቢሮ አመራሮች ተሳትፈዋል።
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የተፈጥሮ ሳይንስ እና ቀመር ኮሌጅ ዲን ቢቂላ ወርቅነህ (ዶ/ር) በፓናል ውይይቱ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ በስንዴ አምራችነት ከዓለም 20ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች።
ሆኖም በስንዴ ምርት ከዓለም ምርጥ አምስት አምራች ሀገራት ውስጥ ሊያስገባ የሚችል አቅም አላት ብለዋል፡፡
እንደ ዶክተሩ ገለጻ፤ ኢትዮጵያ መሰል ምርቶቿን ለማሳደግ የአረንጓዴ አሻራ ሥራዎችን አጠናክራ እየሠራች ትገኛለች።
በምርታማነት ላይ ተግዳሮቶችን የሚደቅኑ እንደ አየር ንብረት ለውጥ አይነት ፈተናዎች ሊቀረፉ የሚችሉት በአረንጓዴ አሻራ መሆኑን ጠቁመዋል።
ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የምታበረክተው 0.02 በመቶ ብቻ መሆኑን ጠቅሰው፤ የአየር ንብረት ለውጡ የሚመጣው ያደጉ ሀገራት በሚለቁት በካይ ጋዝ ሆኖ፣ በአየር ንብረት ለውጥ ኢትዮጵያ ትፈተናለች ብለዋል።
ኢትዮጵያ እንደሀገር ይሄንን በመረዳት አረንጓዴ አሻራ የሚል መርሀግብር አስጀምራ በዚህ ንቅናቄም የደን ሽፋንን በመጨመር ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የግብርናን ዘርፍ ለመገንባት እየሰራች እንደሆነ ተናግረዋል።
ይህም የምርታማነት አቅሟን የሚያሳድግ እንደሆነ አስረድተዋል።
ጋዜጣ_ፕላስ
