በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ሕገ መንግሥት ማሻሻያ ላይ አቤቱታ ካቀረቡ በኋላ በቁጥጥር ስር የዋሉት በክልሉ ምክር ቤት የተቃዋሚው ቦሮ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ቦዴፓ) ተመራጭ አቶ ዮሐንስ ተሰማ፤ የአምስት ዓመት ከ10 ወር ጽኑ እስራት እና የ15 ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣት እንደተፈረደባቸው አንድ የቦሮ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ አመራር ለአዲስ ስታንዳርድ አረጋገጡ።
የአሶሳ ከተማ ከፍተኛ ፍርድ ቤት በአቶ ዮሐንስ ላይ የቅጣት ውሳኔውን ያስተላለፈው ከአምስት ዓመት በፊት ተቋርጦ በነበረው “ከሊዝ አዋጅ የከተማ መሬት አስፋፍቶ በመያዝ” ክስ መሆኑን እኚህ አመራር ገልጸዋል።
ቀደም ሲል በ2011 ዓ.ም በፖለቲካ ምክንያት እሳቸውን ጨምሮ [አቶ ዮሐንስን] ተይዘን ነበረ ያሉት አመራሩ በ2012 ዓ.ም ክሱ ተቋርጦ እንደነበረ አስታውሰዋል።
ይሁን እንጂ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ሕገ መንግሥት ማሻሻያ ላይ አቤቱታ ካቀረቡ በኋላ “በሽብር እና ህገመንግስታዊ ስርዓቱን በማፍረስ” በሚል በክልሉ የምክር ቤት አባልነታቸው የነበራቸው ያለመከሰስ መብታቸው ተነስቶ በቁጥጥር ውስጥ መዋላቸውን አንስተዋል።
“ፖሊስም ሆነ አቃቤ ህግ በዚህ ክስ [በሽብር] መረጃ በማጣታቸው የተነሳ ከዚህ ቀደም ተከሰውበት እና ተቋርጦ የነበረውን ከሊዝ አዋጁ ጋር ተያይዞ የቀረበባቸውን ክስ እንዲቀጥል ተደርጓል” የሚሉት አመራሩ ፍርድ ቤት ሐምሌ 28 ቀን 2017 ዓ.ም በዋለው ችሎት ጥፋተኛ ተብለው በትናንትናው ዕለት የመጨረሻ ውሳኔ እንደተሰጠበት አመልክተዋል።
