የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ባካሄደው የ500 ሚሊዮን ዶላር ልዩ የውጭ ምንዛሬ ጨረታ ከንግድ ባንኮች የ710 ሚሊዮን ዶላር ከፍተኛ ፍላጎት መቅረቡን አስታወቀ።
በዚሁ ነሐሴ 14 ቀን 2018 ዓ.ም. በተካሄደው የገንዘብ ፖሊሲ ትግበራ ልዩ ጨረታ፣ ከተሳተፉት 22 ንግድ ባንኮች ውስጥ 21ዱ የዶላር ድልድል ማግኘት ችለዋል። የቀረበው የፍላጎት መጠን ባንኩ ለሽያጭ ካቀረበው በ210.14 ሚሊዮን ዶላር ብልጫ ያለው ሲሆን፣ ይህም የ142 በመቶ ያህል ከፍተኛ ፍላጎት እንደነበር ያሳያል።
በዚሁ መሰረት ማዕከላዊ ባንኩ ባከናወነዉ ጨረታው የአንድ ዶላር አማካኝ ዋጋ 160.21 ብር ሆኖ ተመዝግቧል። ይህም ነሐሴ 6 ቀን 2018 ዓ.ም ከተካሄደው መደበኛ ጨረታ (161.80 ብር) ጋር ሲነጻጸር የብር የመግዛት አቅም በአንድ በመቶ ገደማ ከዶላር አንፃር ተጠናክሯል።
ይህ ልዩ ጨረታ ብሔራዊ ባንክ በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ ሩብ ዓመት ለማካሄድ ካቀዳቸው አራት መደበኛ የ125 ሚሊዮን ዶላር ጨረታዎች ውጪ የተካሄደ ሲሆን፣ ቀጣዩ መደበኛ ጨረታ በነሐሴ 20 ቀን ይካሄዳል ተብሎ ይጠበቃል።
