ዛሬ ረፋድ ላይ በሆለታ ወልመራ ወረዳ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ውስጥ በተፈጸመ ጥቃት፣ የዕለቱን የችሎት ውሳኔ በማንበብ ላይ የነበሩ ዳኛ እና አንዲት ተከራካሪ ህይወታቸው ማለፉን አክሰስ ቱ ጃስቲስ ኢኒሼቲቭ – ኢትዮጵያ (Access to Justice Initiative – Ethiopia) አስታወቀ።
እንደ ምንጩ መረጃ፣ የቤተሰብ ክርክር ጉዳይን በመመልከት ላይ የነበሩት ዳኛ ወርቄ ፈካንሳ የፍርድ ውሳኔውን እያነበቡ ባሉበት ወቅት፣ ተከሳሹ በድንገት ባወጣው ሽጉጥ ዳኛዋን በጥይት በመምታት ህይወታቸውን ቀጥፏል። በዚሁ አጋጣሚ በችሎቱ ላይ በጉዳዩ ላይ ይከራከሩ የነበሩት (ተከራካሪዋ) በተመሳሳይ ሁኔታ በተከሳሹ በተተኮሰ ጥይት ወዲያውኑ ህይወታቸው አልፏል።
የሕግ ባለሙያዎችና ማህበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚዎች ድርጊቱን በጽኑ ያኮነኑ ሲሆን፣ ዳኞችና የሕግ ባለሙያዎች በሥራ ገበታቸው ላይ አስተማማኝ የደህንነት ጥበቃ ሊደረግላቸው እንደሚገባ በርካቶች በመጻፍ ላይ ይገኛሉ።
“አንድ ግለሰብ ታጥቆ ወደ ፍርድ ቤት አዳራሽ መግባት መቻሉ፣ የፍርድ ቤቶቻችን የጸጥታና የፈተሻ አሰራር ምን ያህል ደካማ እንደሆነ በአሳዛኝ ሁኔታ አሳይቷል” በማለት አክሰስ ቱ ጃስቲስ ኢኒሼቲቭ የድርጊቱን አሳሳቢነት ገልጿል።
አክሰስ ቱ ጃስቲስ ኢኒሼቲቭ – ኢትዮጵያ ለዳኛ ወርቄ ፈካንሳ ቤተሰቦች፣ ለሟች ተከራካሪ ወዳጅ ዘመዶች እንዲሁም ለመላው የፍትሕ አካላት መጽናናትን ተመኝቷል።
