የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን ከዕፅዋት የሚዘጋጅ የአውሮፕላን ነዳጅ ለመጠቀም የሚያስችል ዘላቂ የአቪዬሽን ነዳጅ ላይ የተሠራ የአዋጭነት ጥናት ሪፖርት ኅዳር 18 ቀን 2018 ዓ.ም. ሲያቀርብ የተገኙት የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ (ዶ/ ር)፣ በነዳጅ የሚሠሩ ተሽከርካሪዎች የሚለቁት በካይ ጋዝ ምን ያህል መሆን እንዳለበት የሚወስን ስታንዳርድ መዘጋጀቱን ገልጸዋል፡፡
ሚኒስቴሩ ስታንዳርዱን ያዘጋጀው ከኢትዮጵያ የደረጃዎች ኢንስቲትዩት ጋር መሆኑንና አሽከርካሪዎች በተዘጋጀው ስታንዳርድ መሠረት የማይጠቀሙ ከሆነ እንደሚታገዱ፣ በተለይም ለረዥም ጊዜ ያገለገሉና ሞተራቸው ያረጀ ተሽከርካሪዎች የሚለቁት በካይ ጋዝ ከፍተኛ በመሆኑ ካላስተካከሉ እንደሚታገዱ አስታውቀዋል፡፡
‹‹ተሽከርካሪዎች የሚለቁት የጋዝ መጠን በሕጉ ከተቀመጠው በላይ መብለጥ እንደሌለበት መጠኑን ያስቀመጠ የሕግ ድንጋጌ ተዘጋጅቷል፡፡ ይህ ሕግ ሥራ ላይ መዋሉ በካይ ጋዝ እንዲቀንስ ያደርጋል፡፡ ስለዚህ በቅርቡ ሥራ ላይ ማዋል እንጀምራለን፤›› ብለዋል፡፡
ስታንዳርዱን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል ቴክኖሎጂ መኖሩን የገለጹት ሚኒስትሩ፣ አሽከርካሪዎች ቴክኖሎጂውን መጠቀምና ስታንዳርዱን ማሟላት ግዴታቸው እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
Reporter
