የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ደንብ ማስከበር ባለስልጣን ከአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ጋር በመተባበር፣ በካይ ቆሻሻ ወደ ወንዝ በመልቀቁ ምክንያት በአርማወር ሐንሰን የምርምር ተቋም (AHRI) ላይ አንድ ሚሊዮን ብር መቅጣቱን አስታውቋል። ይህ እርምጃ የተወሰደው፣ ከተመሳሳይ ወንዝ መበከል ጋር በተያያዘ ከሁለት ቀናት በፊት አለርት ሆስፒታል ተመሳሳይ ቅጣት ከተጣለበት በኋላ ነው።
ባለስልጣኑ ዛሬ እንዳስታወቀዉ፤ አርማወር ሐንሰን የምርምር ተቋም (AHRI) በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ወረዳ 1፣ ዘነበ ወርቅ አካባቢ የሚገኝ ሲሆን፣ የፍሳሽ ቆሻሻ ማስወገጃ መስመሩን ከወንዝ ጋር በማገናኘት ብክለት ፈጽሟል።
በ ጥቅምት 26 ቀን 2018 ዓ.ም. የመንግስት የጤና ተቋም የሆነው አለርት ሆስፒታል ደግሞ በተመሳሳይ በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ውስጥ በወንዝና በወንዝ ዳርቻ በካይ ቆሻሻ በመልቀቁ ምክንያት አንድ ሚሊዮን ብር ቅጣት ተጥሎበት አስተዳደራዊ እርምጃ እንደተወሰደበት ይታወቃል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ደንብ ማስከበር ባለስልጣን፣ የግንዛቤ ፈጠራ ሥራዎች ቢሰሩም ከህገ-ወጥ ተግባራት የማይታቀቡ ግለሰቦች እና ድርጅቶች ላይ የሚወስደው አስተዳደራዊ እርምጃ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አሳስቧል።
