የማለፊያ ውጤት 50 በመቶ እንዲሆን ተወስኗል
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ የአጠቃላይ ካውንስል አባላት የ2017 የትምህርት ዘመን የ6ኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተና የማለፊያ ውጤት 50 በመቶ እንዲሆን በዛሬው ዕለት ወስነዋል።
የከተማ አስተዳደሩ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ዘላለም ሙላቱ በአዲሱ ስርዓተ ትምህርት መሰረት በከተማ አስተዳደሩ የ6ኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተና ከ2015 የትምህርት ዘመን ጀምሮ መሰጠቱን አስታውሰው፤ በ2017 የትምህርት ዘመን ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት በመስራቱ የተመዘገበው ውጤት አበራታች መሆኑን ተናግረዋል።
አያይዘውም በ2017 ዓ.ም የሒሳብና እንግሊዘኛ ትምህርትን ለማሻሻል ተግባራዊ የተደረገው ስትራቴጂ በተማሪዎች ውጤት መረጋገጡን የገለጹ ሲሆን፤ በተጨማሪም የከተማ አስተዳደሩ በትምህርት ዘርፉ ላይ ባደረገው ትኩረት ውጤቱ መመዝገቡን ተናግረዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ ዲናኦል ጫላ በበኩላቸው፤ በከተማ አስተዳደሩ 79 ሺሕ 34 ተማሪዎች ፈተናውን መውሰዳቸውን ገልጸዋል፡፡
የ6ኛ ክፍል ከተማ አቀፍ ፈተና ከሰኔ 10 እስከ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ድረስ፤ በከተማ አስተዳደሩ በሚገኙ 192 የመፈተኛ ጣቢያዎች ለተከታታይ ሦስት ቀናት መሰጠቱ ይታወሳል።
