የዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ብሔራዊ የህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ኢኳተር በሚባለው ግዛት 52 ሰዎችን የገደለውና 1000 ሰዎችን ያጠቃው በሽታ ወባ እንደነበር በላብራቶሪ ምርመራ ማረጋገጣቸውን ይፋ አድርገዋል።
በተጠቂዎች ላይ የትኩሳት፣የድካም፣የማስመለስና ክብደት የመቀነስ ምልክቶች ታይተው የነበረ ሲሆን በሽታው ወባ ወይም የምግብ መመረዝ ሊሆን እንደሚችል ተገምቶ ነበር።
ከተጠቂዎች በተወሰዱ ናሙናዎች በተደረገ የላብራቶሪ ምርመራ በሽታው ወባ መሆኑ የተረጋገጠ ሲሆን በምግብ፣ውሃና መጠጥ ናሙናዎች ላይ ግን አሁንም የላብራቶሪ ምርመራ እየተደረገ ነው።
በየካቲት ወር መጨረሻ ኢኳተር በምትባለው ግዛት በወቅቱ ባልታወቀ በሽታ 52 ሰዎች ሞተው የነበረ ሲሆን የአለም ጤና ድርጅት ይዞት በወጣው መረጃም በሽታው እስከ አንድ ቀን ውስጥ ሲገድል ነበር ብሏል።
በወቅቱ ተጠቂዎቹ ከወባ እና ምግብ መመረዝ በተጨማሪ በኢቦላና ማርበርግ ተይዘው ሊሆን እንደሚችልም ተገምቶ ነበር።
የአለም 12 በመቶ የወባ በሽታ ተጠቂዎችን የምታስመዘግበው ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ያለችበት የፀጥታ ችግር እና ያሏት ደካማ የጤና መሰረተ ልማቶች በሽታውን ለመቆጣጠር ፈታና መሆናቸውም ተገልጿል።
Source : CGTN Africa
