የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያጸደቀውን አዲሱን የመረጃ ነጻነት አዋጅ ቁጥር 1427/2018 አስመልክቶ የሕዝብ ዕንባ ጠባቂ ዋና ዕንባ ጠባቂ ወ/ሮ ስመኝ ውቤ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
በአዲሱ አዋጅ መሠረት፣ በፍርድ ቤት የጥፋተኝነት ውሳኔ ሳይሰጥ ማንኛውንም ጋዜጠኛ፣ ዋና አዘጋጅ ወይም ከጉዳዩ ጋር የተያያዘ ሰውን ለምርመራም ሆነ ለሌላ ምክንያት ማሰር በጥብቅ የተከለከለ ነው።
በተጨማሪም መረጃን በቅን ልቦና ያሰራጨ የሜድያ ባለሙያ ከተጠያቂነት ነጻ ሲሆን፣ መረጃን ሆን ብሎ ያጠፋ፣ የደለዘ፣ የደበቀ ወይም ሙስናን ለመሸፈን በሚስጥር የያዘ አካል እስከ 5 ዓመት በሚደርስ እስራት ወይም በ100 ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣት እንደሚቀጣ ተደንግጓል።
አዲሱ አዋጅ ከቀድሞው በተለየ መልኩ የመንግሥት ተቋማትን ብቻ ሳይሆን ትላልቅ የግል ድርጅቶችን እና ከመንግሥት ጋር በጥምረት የሚሰሩ አካላትንም መረጃ የመስጠት ግዴታ ጥሎባቸዋል።
ማንኛውም ተቋም ይህንን ተግባራዊ ለማድረግ የመረጃ ኃላፊ መመደብ ያለበት ሲሆን፣ የቀረቡለትን የጥያቄና ምላሽ ዓመታዊ ሪፖርቶች ለዕንባ ጠባቂ ተቋም ማቅረብ ይኖርበታል።
የመረጃ ጥያቄን የከለከለ ወይም ሐሰተኛ መረጃ የሰጠ አካል እስከ 1 ዓመት በሚደርስ ቀላል እስራትና የገንዘብ መቀጮ እንደሚቀጣ የገለጹት ወ/ሮ ስመኝ፣ አዋጁን ሙሉ በሙሉ ለማስፈጸም የሚያስችሉ ደንቦችና መመሪያዎች መዘጋጀታቸውንም አክለዋል።
