በጤና ሚኒስቴር በ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት ከ100 ሚሊዮን በላይ ኮንዶም ግዥ ለመፈጸም መታቀዱን፤ በሚኒስቴሩ የኤች አይቪ መከላከልና መቆጣጠር ዋና መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ፍቃዱ ያደታ ተናግረዋል።
አክለውም፤ በአዲስ አበባና ጋምቤላን ጨምሮ የኤች አይቪ ኤድስ ስርጭት በአንዳንድ ክልሎች አሁንም ስጋት መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ወጣቶች የበለጠ ተጋላጭ መሆናቸውን አንስተው፤ አስቀድሞ የመከላከል፣ የመታቀብ እና የመወሰን መርሆችን ተግባራዊ እየተደረጉ አለመሆናቸውን አስረድተዋል፡፡
የማህበረሰቡ ግንዛቤ ከማነሱ በተጨማሪ፤ ተቋማት ኮንዶምን በማከፋፈል ረገድ ክፍተት እንዳለባቸውም ተናግረዋል፡፡
በኢትዮጵያ የኤች አይቪ ኤድስ ስርጭትን በ2030 ከ0 ነጥብ 1 በመቶ በታች ለማድረግ እየተሰራ መሆኑ የተገለጸ ቢሆንም፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ605 ሺሕ በላይ ዜጎች ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ እንደሚገኝ የጤና ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል፡፡
(አሐዱ ሬዲዮ)
