አፍሪካ በየዓመቱ እስከ 200 ቢሊዮን ዶላር የሚደርስ ኢኮኖሚያዊ ኪሳራ እንደምትደርስባት ዓለም ባንክ ባወጣው ሪፖርት አመልክቷል።
ይህ ኪሳራ የሚከሰተው በቂ የንፅህና አጠባበቅ አገልግሎት ባለመኖሩ ሲሆን፣ የዓለም ባንክ በአህጉሪቱ በዚህ ዘርፍ ላይ የሚደረግ ኢንቨስትመንት አጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርትን (GDP) እስከ 5 በመቶ ሊያሳድግ እንደሚችል ገልጿል።
ሪፖርቱ አክሎ እንደገለፀው፣ በአለም አቀፍ ደረጃ ከየአምስት ሰዎች መካከል ሁለት የሚሆኑት አስተማማኝ የንፅህና አገልግሎት አያገኙም፤ ይህም በተለይ በአፍሪካ እንደ ኮሌራ እና ተቅማጥ ያሉ በሽታዎች እንዲስፋፉ ምክንያት ሆኗል።
በተለይ በከተሞች ውስጥ ባሉ ሰፈራዎች የፍሳሽ ማስወገጃ ስርዓት አለመኖር ችግሩን የበለጠ እንዳወሳሰበው ተመላክቷል።
የዓለም ባንክ በሪፖርቱ ላይ የንፅህና አጠባበቅ አገልግሎቶችን ማሻሻል የህዝብ ጤናን ከመጠበቅ ባሻገር፣ የኢኮኖሚ ምርታማነትን እንደሚያሳድግ እና ለትምህርት ጥራት መሻሻል ወሳኝ ሚና እንደሚጫወት አብራርቷል።
ባንኩ የአፍሪካ መንግስታት እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በአፋጣኝ ለንፅህና ዘርፍ ቅድሚያ በመስጠት በአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ የማይፈጠርባቸውን ዘመናዊ መሠረተ ልማቶችን እንዲገነቡ ጥሪ አቅርቧል። ይህም የረዥም ጊዜ የኢኮኖሚ፣ የማህበራዊ እና የአካባቢ ጥበቃ ጥቅሞችን እንደሚያስገኝ አሳስቧል።
CapitalNews
