ብርሃን ገበያ 900 ሚሊዮን ብር የተመደበበት 10 ሺህ ስራ ፈላጊዎችን የአነስተኛ ሱፐር ማርኬት ባለቤት የሚያደርግ ፕሮጀክት ይፋ አድርጓል
ብርሃን ገበያ ከጤግሮስ ትሬዲንግ በጋራ በመሆን በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ 10 ሺህ ለሚሆኑ ስራ ፈላጊዎች የአነስተኛ ሱፐር ማርኬት ባለቤት የሚያደርግ በአምስት ዓመት ውስጥ ደግሞ ወደ ከፍተኛ የገበያ ማዕከላት ባለቤትነት የማሳደግ የስራ ዕቅድ ይዞ እየሰራ እንደሚገኝ ተገልጿል ።
በአጠቃላይ በኦሮሚያ እና በሌሎች ክልል ለበርካታ ወጣቶች ስልጠና በመስጠት የስራ ዕድል መፍጠሩን አቶ ፊሊሞን ካሳሁን የሊንካስ ትሬዲንግ ዋና ስራአስፈጻሚ ለብስራት ሬዲዮ እና ቴሌቪዥን ተናግረዋል ። ተቋሙ በተለያዩ ክልሎች ስልጠና በመስጠት ያለ ምንም መነሻ ወደ ስራው የማስገባት ስራ እንደሚያከናውን ተጠቁሟል። ወጣቶቹ ቅድሚያ መነሻ የሚሰጣቸው ራሱ ድርጅቱ ሲሆን ከቻይና የሚመጡ እና በሀገር ውስጥ የሚመረቱ የስቴሽነሪ እንዲሁም የመጠጥ ዓይነቶችን በመሸጥ ራሳቸውን እንዲችሉ እንደሚያደርግ ተጠቁሟል።
ይህንን ዓላማ ለማሳካት ብርሃን ገበያ ከዳሽን ባንክ ፣ከስንቄ ባንክ ፣ ከኢንሳ እና ከሌሎችም መንግስታዊ እና መንግስታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች ጋር እንደሚሰራ ተነግሯል።ብርሃን ገበያ ፕሮጀክቱን ለማሳካት እንዲሆን 900 ሚሊዮን ብር የተመደበ ሲሆን የእድሉ ተጠቃሚ ለመሆን ንግድ ፍቃድ ያላቸው እና ከወጣቶች እና ስፖርት ቢሮ የድጋፍ ደብዳቤ እንደሚያስፈልግ ተጠቁሟል።
በተጨማሪም አርቲስት ሙሉዓለም ጌታቸው እና ወጣት ቅድስት ሙሉዓለም ለአምስት ዓመት የሚቆይ በየዓመቱ የሚታደስ የአምባሳደርነት ኮንትራት ተፈራርመዋል።
