ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስን ጨምሮ ሦስት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ወደ ሀገር እንዲገቡ ከቅዱስ ሲኖዶስ የቀረበውን ጥያቄ መቀበሉን መንግሥት አሳወቀ።
የመንግሥት ኮሚኒኬሽን አገልግሎት ዛሬ ባወጣው መግለጫ ቅዱስ ሲኖዶስ መንግሥትን እንዲያናግሩ በወከላቸው ብፁዓን አባቶች አማካኝነት ከመንግሥት ጋር ተነጋግረው በተደረገው ስምምነት መሠረት ሦስት ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ከአሜሪካ ወደ ኢትዮጵያ እንዲገቡ መፈቀዱን ገልጿል።
መንግሥት የቀረበውን ጥያቄ እንደተቀበለ አስታውሶ ችግሮች እንዲፈቱ ተቀራርቦ መነጋገር ከሁሉም ተሻለ መፍትሔ መንገድ እንደሆነም በመግለጫው አመላክቷል።
በዚህም መሠረት ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ(ዶ/ር) የኒዎርክና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ፣ ብፁዕ አቡነ ያእቆብ የጆርጅያና አካባቢው ሊቀ ጳጳስ እንዲሁም ብፁዕ አቡነ ቴዎፍሎስ (ዶ/ር) የሰሜን ካሊፎርኒያ እና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በግንቦት 6/2017 ዓ/ም ለሚጀምረው የዚህ ዓመት ርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ እንዲገኙ መንግሥት የሚጠበቀውን ሁሉ እንደሚያደርግ ተገልጿል።
በተፈጠረው ችግር ምክንያት ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ (ዶ/ር) ከጥር 28/2016 ዓ/ም ጀምሮ እንዲሁም ብፁዕ አቡነ ያዕቆብና ብፁዕ አቡነ ቴዎፍሎስ(ዶ/ር) ደግሞ ከግንቦቱ 2016 ዓ/ም ጀምሮ በኢትዮጵያ ተገኝተው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤያትን እንዳልተሳተፉ የሚታወስ ነው።
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ
ስለአንዲት ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን
