ትኩረት ለሴቶችና ለሕፃናት ማኅበር “ድምፅ ለሌላቸው ድምጽ እንሁናቸው” በሚል መሪ ቃል፣ የግንዛቤ ማስጨበጫ እና የእግር ጉዞ መርሃ ግብር ለፊታችን ሚያዝያ 6 ቀን ማዘጋጀቱን በማዕከሉ በሰጠው መግለጫ አስታውቋል።
ማኅበሩ ከተመሠረተ 19 ዓመታትን ያስቆጠረ መሆኑንና አዲስ አበባን ጨምሮ በልዩ ልዩ ክልሎች ለችግር የተጋለጡ ሕፃናትን፣ በድህነት የሚኖሩ ሴቶችን እና ልዩ ድጋፍ የሚሹ የማኅበረሰብ ክፍሎችን በማገልገል ላይ እንደሚገኝ የማኅበሩ መሥራችና ዳይሬክተር ሲስተር አሳየች ይርጋ ገልጸዋል።
አዲስ ለመገንባት በጅምር ላይ ያለውን ባለ ስድስት ወለል ሕንፃ አጠናቆ ለመገንባት 146 ሚሊዮን ብር የሚያስፈልግ መሆኑን ዳይሬክተሯ ተናግረዋል። ሕንፃው በውስጡ ልዩ ፍላጎት ላላቸው ሕፃናት የጤና ማዕከል፣ የመመገቢያና የመዋያ ስፍራ፣ ትምህርት ቤት፣ ለእናቶች የሙያ ማሠልጠኛ ማዕከል እና የገቢ ምንጭ የሚሆኑ የንግድ ማዕከላትን እንደሚይዝም አብራርተዋል።
የጎዳና ላይ የእግር ጉዞው በየዓመቱ ልዩ ፍላጎት ያላቸውን ሕፃናት ለመደገፍና ግንዛቤ ለመፍጠር እንደሚከናወን የገለጹት ዳይሬክተሯ፣ መርሃ ግብሩ በየዓመቱ በአውሮፓውያኑ አቆጣጠር በሚያዝያ (April) ወር ላይ እንደሚካሄድም ጠቁመዋል።
ከእግር ጉዞው የሚገኘው ገቢ ለሕንፃው ግንባታ የሚውል መሆኑን በመጥቀስ፣ የሩጫ ቲሸርቱን በመግዛት ሁሉም የኅብረተሰብ ክፍል ተሳታፊ እንዲሆን ጥሪ አቅርበዋል።
