በዩናይትድ አረብ ኤምሬትስ የአቡ ዳቢ ፖሊስ የተለያዩ አገራት ዜግነት ያላቸው ከ100 በላይ ሰዎች በአገሪቱ ላይ ከሚፈጸመው ጥቃት ጋር በተያያዘ የተለያዩ ቦታዎችን “በመቅረጽ እና አሳሳች መረጃን” በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ በማጋራት መያዙን አሳወቀ።
ፖሊስ በኤክስ ገጹ ላይ ባወጣው መግለጫ የተለያዩ 109 ሰዎች በሕዝቡ መካከል የተሳሳተ አመለካከትን የሚፈጥሩ እና ያልተረጋገጡ ወሬዎችን በማሠራጨት በቁጥጥር ስር አውሏል።
ፖሊስ ጨምሮም ማኅበራዊ ሚዲያን ተገቢ ላልሆነ ዓላማ የሚጠቀሙ ሰዎችን በመከታተል የአገሪቱ የደኅንነት ባለሥልጣን አስፈላጊው ሕጋዊ እና አስተዳደራዊ እርምጃ እንደሚወሰድ አስታውቋል።
የአገሪቱ ዜጎች ወቅታዊ ሁኔታዎችን በተመለከተ ከሚመለከታቸው አካላት እና ከሚታመኑ ምንጮች ብቻ መረጃ እንዲያገኙ በማሳሰብ የሕዝብ ጥቅምን እና አሠራሮችን በማክበር ከአንዳንድ ቦታዎች “ፎቶ ከማንሳት እና ቪዲዮ ከመቅረጽ እንዲሁም ከማጋራት እንዲቆጠቡ” አሳስቧል።
