የአሜሪካው ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ የአሜሪካ መከላከያ ኃይል በኢራን ሦስት የኒውክሌር ተቋማት ላይ የቦምብ ድብደባ መፈፀሙን ተናገሩ።
ፕሬዚደንቱ ለመካከለኛው ምሥራቅ ግጭት የሁለት ሳምንት ጊዜ ሰጥተው የነበረ ቢሆንም፣ ይህንን በተናገሩ በሁለተኛው ቀን ጥቃት ፈጽመዋል።
ይህ የአሜሪካ ጥቃት በኢራን እና በእስራኤል መካከል ያለውን ግጭት እንዳያባብሰው ተሰግቷል።
ዶናልድ ትራምፕ ከጥቃቱ በኋላ በዋይት ሐውስ በሰጡት አጭር መግለጫ “አስታውሱ፣ በርካታ ዒላማዎች ገና ይቀሩናል። በሁሉም መመዘኛ የዛሬው ምሽቱ ከባዱ እና ደግሞ በጣም አደገኛው ነበር” ብለዋል።
ፕሬዚደንቱ በዚሁ ንግግራቸው “ሠላም በፍጥነት የማይመጣ ከሆነ ወደ ሌሎቹ ዒላማዎችቻው በፍጥነት እና በክህሎት እንሄዳለን” ሲሉ ዝተዋል።
ዛሬ አሜሪካ ጥቃት ከፈጸመችባቸው የኒውክሌር ተቋማት መካከል አንዱ በተራራዎች መካከል የተደበቀው ፎርዶ ይገኝበታል።
በተቋሙ ላይ ስለደረሰው ጉዳት እስካሁን የታወቀ ነገር የለም።
BBC Amharic
