በአማራ ክልል ባለፉት ዓመታት በተከሰተው ግጭት፣ መፈናቀል እና የዝናብ እጥረት ምክንያት እድሜያቸው ከ5 ዓመት በታች ከሆኑ ሕጻናት መካከል 40 በመቶ ያህሉ ለመቀንጨር ችግር መጋለጣቸው የክልሉ ጤና ቢሮ አስታውቋል።
በቢሮ የስርዓተ ምግብ የፕሮግራም አስተባባሪ ስሜነህ ወርቁ፤ “በተለይ የምስራቅ እና ምዕራብ አማራ አካባቢዎች የሚገኙ ሕጻናት ከፍተኛ ችግር ውስጥ ይገኛሉ” ሲሉ ተናግረዋል።
ችግሩን ለማቃለል ከአጋር ድርጅቶች ጋር በመሆን ከእርግዝና ክትትል ጀምሮ እናቶች እና ሕጻናት የተመጣጠነ ምግብ እና የሕክምና ክትትል ይደረግ እንደነበረ አስታውሰው፤ በአንዳንድ አካባቢዎች ላይ ባለው የጸጥታ ችግር ምክንያት እርዳታው እየቀነሰ መሆኑን ተናግረዋል።
የክልሉ የስርዓተ ምግብ የፕሮግራም አስተባባሪ አክለውም፤ ወላጆች ስለመቀንጨር ያላቸው ግንዛቤ አነስተኛ መሆኑ ችግሩን ካባባሱ ሰበቦች መሐከል አንዱ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
“ለክልሉ የሚመደበው የጤና በጀት አነስተኛ መሆኑ፣ በግጭት ምክንያት ጥቂት የማይባሉ የጤና ተቋማት ላይ ጉዳት መድረሱ፣ ደግሞ በፍጥነት የማስተካከያ እርምጃዎች መውሰድ እንዳይቻል አድርገዋል” ተብሏል፡፡
