ኢትዮጵያዊው የህግ ባለሙያ አቶ ቴዎድሮስ ጌታቸው የአፍሪካ የጠበቆች ማህበራት ህብረት (PALU) ፕሬዚደንት ሆነው ተመረጡ።
ይህ ምርጫ በአቢጃን፣ አይቮሪ ኮስት እየተካሄደ ባለው 15ኛው የPALU መደበኛ ጉባኤ ላይ የተከናወነ ሲሆን፣ አቶ ቴዎድሮስ የምስራቅ አፍሪካን ክልል ወክለው ይህን ትልቅ የአህጉር አቀፍ ተቋም ለመምራት የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊ እና የመጀመሪያው የምስራቅ አፍሪካዊ ዜጋ መሆናቸው ተጠቁሟል።
54 የአፍሪካ ሀገራት የጠበቆች ማህበራትን እና 8 አካባቢያዊ ተቋማትን በአባልነት የያዘው PALU፣ በአፍሪካ ውስጥ ካሉት ግዙፍ እና ቀዳሚ የህግ ተቋማት አንዱ ነው። አቶ ቴዎድሮስ ከሰጡት ድምጽ ውስጥ ከ3/4ኛ በላይ ድምጽ በማግኘት በቀጣዮቹ ሶስት ዓመታት ድርጅቱን ይመራሉ ተብሏል።
በመጨረሻው ዙር ምርጫ የተፎካካሪያቸው አልጄሪያዊቷ ወ/ሮ አይሻ ቡዳይፍ፣ የPALU የሰሜን አፍሪካ ምክትል ፕሬዚደንት የነበሩ ሲሆን፣ ከ1/3ኛው የአባል ሀገራት ድምጽ በማግኘት ተሸንፈዋል።
አቶ ቴዎድሮስ ለሦስት ዓመታት ያህል ተቋሙን በመምራት ላይ የነበሩትን ካሜሩናዊውን ሚስተር ካሪ አብዱልባጎይን ይተካሉ።
ከፕሬዚደንታዊ ምርጫው በተጨማሪ፣ ጉባኤው አምስት ምክትል ፕሬዚደንቶችን (የምስራቅ፣ ምዕራብ፣ መካከለኛው፣ ሰሜን እና ደቡብ አፍሪካ ክልሎችን የሚመሩ)፣ የድርጅቱ ዋና ፀሐፊን እና ዘጠኝ ሌሎች የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባላትን መርጧል።
