የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) ዓለምአቀፍ መገናኛ ብዙኃን የአፍሪካ ህብረት ጉባኤን ሽፋን በሚሰጡበት ወቅት በኢትዮጵያ የሚፈጸሙ ከፍተኛ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶችን በመዘገብ ለዓለምአቀፉ ማህበረሰብ ተደራሽ እንዲያደርጉ ጠይቋል፡፡
ፓርቲው ባወጣው መግለጫ መገናኛ ብዙኃኑ በኢትዮጵያ የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤን በሚዘግቡበት ወቅት “የእውነት ፈላጊነትን፣ የነጻነትን እና ለሕዝብ ተጠያቂ የመሆንን መሠረታዊ የጋዜጠኝነት መርሆች እንዲያከብሩ” አሳስቧል።
ኢሕአፓ በአዲስ አበባ የሚካሄዱ ዲፕሎማሲያዊ መድረኮች የዓለምን ትኩረት ቢስቡም፤ “በአማራ፣ በኦሮሚያ፣ በትግራይ እና በሌሎች አካባቢዎች የሚገኙ ማህበረሰቦች የሰው አልባ አውሮፕላን (ድሮን) ጥቃቶችን እና የሲቪል ሰዎችን ሞት ጨምሮ አሁንም ለጥቃት እየተጋለጡ እንደሚገኙ” አመልክቷል።
እነዚህን እውነታዎች መርምሮ አለመዘገብ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ድምፅ እንዳይሰማ እና ስቃያቸው እንዳይታይ የማድረግ አደጋ አለው ሲልም አስጠንቅቋል፡፡ በዚህም እነዚህ ዓለምአቀፍ መገናኛ ብዙኃን ቢያደርጓቸው ያለውን አምስት ነጥቦች ዘርዝሯል፡፡
“ከአዲስ አበባ ውጭ ስላሉ ቀጣይ ጥቃቶች የተረጋገጡ መረጃዎችን እንዲፈልጉ፤ ጥቃት ከደረሰባቸው ማህበረሰቦች፣ ከሰብአዊ ረዳት ሰራተኞች እና ከገለልተኛ ታዛቢዎች ጋር እንዲነጋገሩ፤ ጋዜጠኞች፣ ፖለቲከኞች፣ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች እና በሺዎች የሚቆጠሩ ንጹሃን ዜጎች በመንግስት አማካኝነት ለዓመታት ያለ አግባብ ታስረው የሚገኙባቸውን እስር ቤቶች እንዲጎብኙ፤ በጥንቃቄ፣ በሚዛናዊነት እና በድፍረት እንዲዘግቡ፤ የሰላማዊ ሰዎች ስቃይ በመሪዎች ስብሰባ እና በአዲስ አበባ ደማቅ መብራቶች እንዳይሸፈን እንዲያደርጉ” ጥሪ አቅርቧል።
