የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራቅቺ፤ ስልታዊ ጠቀሜታ ያለው የሆርሙዝ የባህር ስርጥ ክፍት ቢሆንም፣ “ለኢራን ጠላቶችና ለባልደረቦቻቸው” ግን ዝግ መሆኑን ገለጹ።
ሚኒስትሩ ዛሬ በሰጡት መግለጫ፤ የባህር ስርጡ ለዓለም አቀፍ የንግድ መርከቦች ዝውውር ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ ጠቁመው፣ ነገር ግን ከኢራን ጋር ግጭት ውስጥ ላሉ ወገኖችና ለደጋፊዎቻቸው የነዳጅ ጫኝ መርከቦችም ሆኑ ሌሎች የንግድ መርከቦች ማለፊያ እንደማይሆን በግልጽ አስታውቀዋል።
ይህ የአባስ አራቅቺ መግለጫ የወጣው በኢራን፣ በእስራኤልና በአሜሪካ መካከል ያለው ቀጠናዊ ውጥረት በከፍተኛ ሁኔታ በጨመረበትና የባህር ላይ ደህንነት ስጋት በገነነበት ወቅት ነው።
የኢራን ባለስልጣናት ቀደም ሲል የባህር ስርጡን የመዝጋት እቅድ እንደሌላቸው ሲገልጹ ቢቆዩም፣ አሁን ግን “ለጠላቶቻችን” በሚል የለየለት ክልከላ መጣሉ ቀጠናዊ ፍጥጫውን ወደ አዲስ ምዕራፍ ሊያሸጋግረው እንደሚችል ተሰግቷል።
የሆርሙዝ የባህር ስርጥ በዓለም ላይ ከሚዘዋወረው የነዳጅ ምርት ውስጥ ሲሶው የሚያልፍበት ወሳኝ መስመር ሲሆን፣ በዚህ ስርጥ ላይ የሚደረግ ማንኛውም አይነት የትራፊክ መስተጓጎል በዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋና በኢኮኖሚው ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ እንደሚያሳድር ይታወቃል።
ኢራን ይህን እርምጃ የወሰደችው በአገሪቱ ላይ ለሚሰነዘሩ ጥቃቶችና ለሚጣሉ ማዕቀቦች እንደ ግፊት መጠቀሚያ እንደሆነ ዲፕሎማሲያዊ ምንጮች እየገለጹ ይገኛሉ።
