የ2017 በጀት ዓመት በመንግሥት እና በግል ጤና ተቋማት ለነበረው የመድኃኒት አቅርቦት በአጠቃላይ ከ1 ነጥብ 1 ቢሊየን ዶላር በላይ ወጪ መደረጉን የኢትዮጵያ መድኃኒት ምርት እና የሕክምና መገልገያ አምራቾች ማህበር አስታውቋል፡፡
የማህበሩ ፕሬዝዳት ዶክተር ዳንኤል ዋክቶሌ “በበጀት ዓመቱ ኢትዮጵያ ከ1 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር በላይ ለመድኃኒት ፍጆታዋ ወጪ አድርጋለች” ብለዋል፡፡ በቀጣይ 3 ዓመታት ውስጥ ዓመታዊ የመድኃኒት ፍጆታው ከ3 ቢሊየን ዶላር በላይ ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል፡፡
በሀገር ውስጥ ያለውን የመድኃት እና የሕክምና መገልገያ ምርቶች አቅርቦትን ወደ 15 ነጥብ 6 ቢሊየን ዶላር እንዲጠጋ ለማስቻል እየተሰራ እንደሚገኝም ገልጸዋል፡፡
ማህበሩ በማምረት ላይ የሚገኘው የመድኃኒት አይነቶች የተለመዱ እና ከዚህ ቀደም የነበሩ እንደሆኑ የገለጹ ሲሆን፤ “በብዛት የሚያስፈልጉትን እና ጥቅም ላይ የሚውሉትን ነው የምናመርተው” ብለዋል፡፡
በሀገር ውስጥ መድኃኒት አምራቾች ይሸፈናሉ ተብለው የተለዩት የመድኃኒት ዓይነቶች 97 እንደሆኑ የተናገሩት የማህበሩ ፕሬዝዳንት፤ ከሕክምና መገልገያ ግብዓቶች የተለዩት ደግሞ 26 መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
እንደ ፕሬዝዳንቱ ገለጻ፤ በጥቅሉ በሀገር ውስጥ የሚሸፈኑ የመድኃኒት አይነቶች እና የሕክምና መገልገያ ግብዓቶች 123 ናቸው፡፡
ባጠቃላይ 255 የመድኃኒት አይነቶች ‘በየጊዜው የሚያስፈልጉ ናቸው’ ተብለው የተለዩ ሲሆን፤ ከእነዚህም ውስጥ 97 የሚሆኑ የመድኃኒት ዓይነቶችን በሀገር ውስጥ ዓምራቾች መሸፈን እንደሚቻል ተናግረዋል፡፡
አክለውም የፋይናንስ እጥረትን በዘላቂነት መፍታት ከተቻለ ሀገር ውስጥ የመድኃኒት እና የሕክምና መገልገያ ግብዓቶችን ማምረት እንደሚቻል ጠቁመዋል፡፡
እንዲሁም በአሰራር ላይ ለውጦች የሚስተዋሉ ከሆነ በመድኃኒት እና በሕክምና መገልገያ ምርቶች ላይ የሚታየውን የአቅርቦት እጥረት መፍታት እንደሚቻል ገልጸዋል፡፡
በሀገር ውስጥ የሚመረቱ መድኃኒቶች በአይነት ተመሳሳይ እንዳይሆኑ እና በሌሎች የመድኃኒት አይነቶች ላይ እጥረት እንዳይከሰት ለማስቻል፤ ተመሳሳይ መድኃኒት የሚያመርቱት ተቋማት ከ4 እንዳይበልጡ መደረጉንም የማህበሩ ፕሬዝዳት ጨምረው ገልጸዋል፡፡
(አሐዱ ሬዲዮ)
