ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ የማርቺንግ ባንድኢዜአ ፌስቲቫል ለመጀመሪያ ጊዜ ትሳተፋለች
ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ የማርቺንግ ባንድ ፌስቲቫል ለመጀመሪያ ጊዜ እንደምትሳተፍ የመከላከያ ሰራዊት ስነ-ልቦና ግንባታ ዋና ዳይሬክተር ሜጄር ጄኔራል እንዳልካቸው ወልደሚካኤል ገለጹ።
በመከላከያ ሚኒስቴር የመከላከያ ሰራዊት ስነ-ልቦና ግንባታ ዋና ዳይሬክተር ሜጄር ጄኔራል እንዳልካቸው ወልደሚካኤል ፌስቲቫሉን አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።
በመግለጫቸውም የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት በሁሉም ዘርፎች ያለውን ተቀባይነትና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ለመጨመር ለሚያስችሉ ስራዎች ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያገኘችውን ተቀባይነት ተከትሎ በዓለም አቀፍ የማርቺንግ ባንድ ፌስቲቫል ተሳታፊ እንድትሆን ከአንድ ዓመት በፊት ጥሪ መቅረቡን አስታውሰዋል።
በዚህም የመከላከያ ኪነ-ጥበባት ዳይሬክቶሬት የማርቺንግ ቡድን በሩሲያ ሞስኮ በሚካሔደው ዓለም አቀፍ ፌስቲቫል ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ እንደሚሳተፍ አስታውቀዋል።
ሃምሳ አባላት የያዘው ማርቺንግ ቡድኑ ዛሬ ምሽት ወደ ሩሲያ ለሚያደርገው ጉዞ አስፈላጊውን ዝግጅት ማጠናቀቁን አብራርተዋል።
ቡድኑ ለሁለት ሳምንታት በሚኖረው ቆይታ የኢትዮጵያን የመከላከያ ሰራዊት ማርቺንግ ብቃትና አቅም ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የሚያስተዋውቅ ስለመሆኑም አንስተዋል ።
ኢዜአ
