ኢትዮጵያ ኤርትራን ጨምሮ ከሌሎች ጎረቤት አገራት የሚቀርቡ የፖሊዮ ቫይረስ ናሙናዎችን ተቀብላ ምርመራ እንደምታደርግ የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት አስታውቋል፡፡
በኢንስቲዩቱ የፖሊዮ እና መሰል በሽታ የተግባቦት አማካሪ አቶ ግርማ ሀይለማርያም ባለፉት ጊዜያት በሀገሪቱ ከተከሰተው የኮቪድ 19 ወረርሽኝ በኋላ እንደ ሀገር የላብራቶሪ አቅምን የሚያሳድጉ ስራዎች በትኩረት መሰራታቸውን ገልጸዋል፡፡
አሁን ላይ ኢንስቲትዩቱ በፖሊዮ ቫይረስ የተጠቁት ዜጎችን ናሙና በመውሰድ የመመርመር ስራ እንደሚሰራ አስታውቀዋል፡፡
ከዚህም ባለፈ የቫይረሱ አይነት ከየትኛው የፖሊዮ አይነት ጋር ሊገናኝ ይችላል የሚለውን ከሀገር ውስጥ ባለፈ ወደ ውጭ ተልኮ እንደሚመረመር እና እንደሚረጋገጥ አስታውቀዋል፡፡
ኢትዮጵያ ከጎረቤት ሀገራት ሳይቀር የፖሊዮ ናሙና እንደምትቀበል የገለጹት አማካሪው፤ እንደ ማሳያም ኤርትሪያን ጠቅሰዋል፡፡
ባለፉት ጊዜያት ከተከሰተው የኮቪድ 19 ወረርሽኝ እስከ አሁኑ የማል-በርግ ቫይረስ በሀገር ውስጥ ናሙና የመውሰድ እና ምርመራ የማድረግ ስራም እየተከናወነ መሆኑን ነው የገለጹት፡፡
የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ከነገ ጀምሮ ለ3 ቀናት በሚቆይ የዘመቻ የፖሊዮ ክትባት በአገር አቀፍ ደረጃ 25 ሚሊየን የሚሆኑ ህጻናት እንደሚከተቡ ማስታወቁ ይታወሳል፡፡
