እስራኤል እሁድ ዕለት በጋዛ በፈፀመችው ጥቃት በሐማስ የሚመራው የፍልስጤም የአገር ውስጥ ደኅንነት አገልግሎት ከፍተኛ ባለሥልጣን እና ረዳታቸው መገደላቸውን የሕክምና ምንጮችና ፖሊስ ገለጹ።
ሮይተርስ የዜና ወኪል እንደዘገበው ባለሥልጣናቱ ጥቃቱ የተፈፀመባቸው በማዕከላዊ ጋዛ ሰርጥ ዴር አል ባላ ከተማ በተሽከርካሪ እየተጓዙ በነበረበት ወቅት ነው።
በጥቃቱ በማዕከላዊ ጋዛ የሚገኘው የደኅንነት አገልግሎት ኃላፊ ኮሎኔል ዋኤል ኤል ሌዳዊ እና ሜጀር ራምዝ አቡ ዚራቅ ተገድለዋል።
የእስራኤል ጦር ጥቃቱን የፈፀመው በሐማስ ታጣቂዎች ላይ እንደሆነ ከመግለጽ ውጭ የሰጠው ዝርዝር መረጃ የለም።
እስራኤል ባለፉት ወራት ለእስራኤል እና በጋዛ ለሚገኙ ኃይሎቿ ስጋት የደቀኑ የሐማስ ወታደራዊ ክንፍ አባላት ናቸው በሚል ከፍተኛ ባለሥልጣናትን ጨምሮ በርካታ በሐማስ የሚመራው ፖሊስ ኃይል አባላትን ገድላለች።
ሐማስ፣ እስራኤል በፖሊስ ኃይል እና በዋና መሥሪያ ቤቱ ላይ የምትሰነዝረው ጥቃት ትርምስ እና ሥርዓት አልበኝነትን ለመፍጠር እንዲሁም በአሜሪካ አሸማጋይነት ባለፈው ጥቅምት የተደረሰውን የተኩስ አቁም ስምምነት ለመጣስ የታሰበ ነው ብሏል።
