በደራሲ ንጉሤ አየለ ተካ የተፃፈው፣ ከፍተኛ ምርምር የተደረገበት “ኦዛና ምኒልክ” የተሰኘ ድንቅ መፅሐፍ የ ቅዳሜ ሰኔ 28 2017 ዓ.ም ከቀኑ 8 ሰዓት በወመዘክር አዳራሽ ተመርቋል፡፡
ከዚህ ቀደም “ታላቁ ጥቁር” የተሰኘውን ከፍተኛ ተነባቢነትን ያገኘ በዳግማዊ ምኒልክ ዙሪያ ላይ ያተኰረ መፅሐፍ ፅፎ ለንባብ ያቀረበው ንጉሤ አየለ አሁን ደግሞ ከፍተኛ ምርምር በማድረግ “ኦዛና ምኒልክን” ለንባብ አብቅቷል፡፡
“ኦዛና ምኒልክ” ስለ ዳግማዊ ምኒልክ ያልተነገሩ ዕውነታዎችን በዝርዝር የሚያስረዳ ጥልቅ የምርምር ሥራ ሲሆን 460 ገፆችንም ይዟል፡፡ መፅሐፉ፣ ኢትዮጵያ ከ 125 ዐመት በፊት በአሜሪካ ጋዜጦች መልካም ገፅታ የያዘች አገር እንደነበረች የሚያስረዳ ሲሆን ሀጂ አብዱላሂን የመሰሉ የምኒልክ ተወካዮች ደብዳቤ ይዘው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ቴዎዶር ሩዝቬልት ዘንድ መቅረባቸውን ተንትኖ የሚያስረዳ ነው።
በዕለቱ የሥነ ሂስ አቅራቢ ደመላሽ አማረ በኦዛና ምኒልክ ላይ የመፅሐፍ ዳሰሳ ያቀረበ ሲሆን ስለ ዳግማዊ አፄ ምኒሊክም አጭር የድምፅ ዶኪመንተሪ ቀርቧል፡፡
የስታትስቲክስ ባለሙያ ወግ አዋቂው በኃይሉ ገብረመድኅንም ለዛ ባለው አቀራረብ የምኒሊክ ዘመን ላይ አጭር ዲስኩር አቅርቧል፡፡
የዕለቱ የክብር እንግዶች ጄነራል ካሣዬ ጨመዳ፣የሰው ዘር አመጣጥ ተመራማሪዎች ዶክተር ብርሀኔ አስፋው እና ዶክተር ዮናስ በየነ ሲሆኑ በተለይ የአርኪዮሎጂ አጥኚዎቹ ዶክተር ዮናስ እና ዶክተር ብርሀኔ ልዩ ክብር የተሰጣቸው ከመሆኑም በላይ በሙያቸው ላይም ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
ደራሲ ንጉሥ አየለ ተካ፣ ከተወዳጅ ሚድያ “ታላላቆችን እናክብር” የተሰኘውን ሽልማት በዕለቱ የተበረከተለት ሲሆን በመፅሀፍ ምረቃው እና ዝግጅቱ ላይ አስተዋፅዖ ላደረጉም ዕውቅና ተሰጥቷል፡፡
ደራሲ ንጉሤ አየለ ተካ ፣በታላላቅ ቤተ መፅሐፍት ውስጥ ጊዜውን በማሳለፍ አዳዲስ የታሪክ ዕውነቶችን ለመጀመሪያ ጊዜ ለአንባቢ ፅፎ ያቀረበ ሲሆን መኖሪያውንም በአሜሪካን አገር ያደረገ ነው።
ንጉሤ አየለ ተካ፣ ከዚህ ቀደም ሐኖስ ፣የገራዶ ዋሽንት፣ ጣዝማ እና ሌሎች 7 መፅሐፍትን ለንባብ ያበቃ ሲሆን በ1970ዎቹ አጋማሽ ከኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ- ፅሑፍ ክፍልም የተመረቀ ነው፡፡
የመፅሐፍ ምረቃ ሁነት ዝግጅቱ በተወዳጅ ሚድያና ኮምዩኒኬሽን እና በአቶ መሳፍንት አወቀ አስተባባሪነት የተሰናዳ ሲሆን መድረክ መሪውም ዕዝራ እጅጉ ነው።
