በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዝዳንት አቶ አቤ ሳኖ የተመራ ልኡካን ቡድን ከድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ከድር ጁሀር እንዲሁም በአስተዳደሩ ከሚገኙ ከፍተኛ አመራሮች ጋር የስማርት ድሬን ጉዞ ለማፋጠንና ስራዎችን በጋራ ለመስራት በሚቻልባቸው ነጥቦች ላይ መክረዋል።
በዚህም ከንቲባ ከድር ጁሀር ለልኡክ ቡድኑ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
የስማርት ድሬን ጉዞ ለማፋጠን በርካታ ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኝ ከንቲባ ከድር ገልፀው በተለይም የተቋማት አገልግሎት አሰጣጥን ከወረቀት ንክኪ ነፃ በማድረግ ዲጂታላይዝ የማረግ ስራ በተጠናከረ መልኩ እየተሰራ እንደሚገኝ አብራርተዋል።
ከንቲባ ከድር አያይዘውም ሲስተሞችን እርስ በእርስ በማስተሳሰርም ለማህበረሰቡ ጊዜ ቆጣቢና ቀልጣፋ አገልግሎት የመስጠቱ ሂደት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል።
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዝዳንት አቶ አቤ ሳኖ በበኩላቸው ድሬዳዋ በዲጂታሉ ዘርፍ እየሰራች የምትገኛው ስራ በአርአያነት የሚጠቀስ መሆኑን በመግለፅ፤ በቀጣይ በአገልግሎት አሰጣጥ፣ በሰላም እና ፀጥታ፣ በትራንስፖርት ዘርፍ እና በሌሎችም ዘርፎች የተጀመሩ የዲጂታላይዜሽን ስራዎች ተጠናክረው መቀጠል እንደሚገባቸው አመላክተዋል።
ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር የተፈራረሙት የመግባቢያ ሰነድ የዲጂታል ድሬን ግስጋሴ በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያፋጥነው እንዲሁም የተጀመሩ ፕሮጀክቶች በፋይናንስ እጥረት ምክንያት እንዳይስተጓጎሉ እንደሚያግዝ የገለፁት ደግሞ የድሬዳዋ አስተዳደር ሳይንስ ፣ ቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ኤጀንሲ ስራ አስኪያጅ አቶ አብዱልአዚዝ ሻፊ ናቸው።
