በአንድ ቀን ከአንድ ሺህ በላይ ስደተኞች በጀልባ እንግሊዝ መግባታቸው ተሰማ፡፡ የእንግሊዝ መንግስት ‹‹ዋን ኢን፣ ዋን አውት›› በሚል ከፈረንሳይ ወደእንግሊዝ በጀልባ የገቡ ስደተኞችን ወደፈረንሳይ የመመለስ ዘመቻ መጀመሩን ማስታወቁ ይታወሳል፡፡
እስካሁን ባለው መረጃም 3 ሰዎች ወደፈረንሳይ እንዲሳፈሩ ተደርገዋል፡፡ የእንግሊዝ መንግስት ይህ ዘመቻው የስደተኞችን ፍልሰት ለመቀነስ ውጤታማ መሆኑን እየገለፀ ባለበት በዚህ ወቅት ሌላ አስደንጋጭ ክስተት ገጥሞታል፡፡ ትላንት አርብ ከፈረንሳይ የተነሱ ትንንሽ ጀልባዎች ከአንድ ሺህ በላይ ስደተኞችን እንግሊዝ አራግፈዋል፡፡ እንደዘገባዎች ከሆነ ትላንት ይህ ጉዞ የተደረገው በ13 ጀልባዎች ሲሆን እንግሊዝ የገቡት ስደተኞች ቁጥርም 1072 ነው፡፡
አንድ ቀን ይህንን ያህል ቁጥር ያላቸው ስደተኞች ድንበሩን ሲሻገሩም ይህ የመጀመሪያው ነው ተብሏል፡፡ ትላንት እንግሊዝ የደረሱትን ጨምሮ በያዝነው አመት ማለትም 2025 ድንበሩን ያቋረጡት ስደተኞች ቁጥርም 32103 መድረሱን የእንግሊዝ አገር ውስጥ ሚኒስትር አስታውቋል፡፡
የእንግሊዝ መንግስት ባወጣው ‹‹ዋን ኢን ዋን አውት›› ፕሮግራም መሰረት በጀልባ የገቡትን ስደተኞች ወደፈረንሳይ የሚልክ ሲሆን በምትኩ ፈረንሳይ የሚገኙ ስደተኞችን ደግሞ በህጋዊ መንገድ የመቀበል ግዴታ አለበት፡፡ እንግሊዝ እስካሁን 3 ስደተኞችን ወደፈረንሳይ የላከች ሲሆን በዚህ መሰረት በሚቀጥለው ሳምንት ደግሞ 3 ስደተኞችን ከፈረንሳይ ለመቀበል እቅድ ይዛለች፡፡
(ዘ-ሐበሻ ዜና)
