በእንግሊዝ ኒውካስል ከተማ አቅራቢያ ይገኝ የነበረውንና ከ100 ዓመታት በላይ ዕድሜ ያስቆጠረውን ታሪካዊ ዛፍ በቆረጡ ሁለት ሰዎች ላይ የኒውካስል ከተማ ፍርድ ቤት የእስር ቅጣት አስተላልፏል።
ዳንኤል ግራሃም እና አዳም ካሩዘርስ የተባሉት እነዚህ ገለሰቦች ላይ ዛሬ ቅጣቱ የተላለፈው፤ በ2023 ላይ ከሚኖሩበት ከተማ ለአርባ ደቂቃ ያህል ተጉዘው ሲካሞር ጋፕ በመባል የሚታወቀውን ታሪካዊው ዛፍ በማሽን በመታገዝ በመቁረጣቸው ነው።
በወቅቱ አነጋጋሪ በነበረው በዚህ ድርጊት አንደኛው ዛፉን ሲቆርጥ፤ ሌላኛው በተንቀሳቃሽ ስልክ ከቀረፀ በኋላ ቦታውን ለቀው መሄዳቸውን ፖሊስ አስታውቆ ነበር።
የተከሳሾቹ ጠበቃ በበኩሉ የድርጊቱ ፈጻሚዎች ሳያስቡበት በመጠጥ ኃይል ተገፋፍተው ይህን በመፈጸማቸው ይቅርታ ሊደረግላቸው ይገባል ሲል የቅጣት ማቅለያ ቢያቀርብም፤ ጉዳዩን ለወራት ይከታተል የነበረው ፍርድ ቤት ሆን ተብሎ የተፈፀመ የሥርዓት አልበኝነት ድርጊት በመሆኑ የአራት ዓመት ከሶስት ወር እስራት ፈርዶባቸዋል።
አካባቢውን የጎበኙ ሁሉ ፎቶ ይነሱበት የነበረው ተወዳጅ ዛፍ በእንግሊዝ በሚገኙ የተለያዩ ፖስተሮች ላይ የሚገኝ የአካባቢው ልዩ ምልክትና ቅርስ የነበረ ዛፍ ነው።
