በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ዜጎች የመምረጥ መብታቸውን እንዲጠቀሙ ለማበረታታት፣ ከ180 በላይ የሲቪል ማኅበራት ድርጅቶች የመራጮች ትምህርት ለመስጠት የሚያስችላቸውን ፈቃድ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ማግኘታቸውን የኢትዮጵያ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት አስታውቋል።
ድርጅቶቹ ፈቃዱን የወሰዱት በሁሉም ምርጫ የሚካሔድባቸው የኢትዮጵያ ክልሎች ተሰማርተው መራጮችን የማንቃት እና መብታቸውን እንዲጠቀሙ የማበረታታት ትምህርት እንዲሰጡና ሂደቱን እንዲታዘቡ እንደሆነ ተገልጿል።
የኢትዮጵያ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት ዋና ዳይሬክተር አቶ አህመድ ሁሴን፡ “ፈቃድ ከወሰዱት ድርጅቶች መካከል 34ቱ የፋይናንስ ድጋፍ አግኝተው ወደ ማስተማር ሥራ የሚያስገባቸውን ዝግጅት በማጠናቀቅ ላይ ናቸው” ያሉ ሲሆን ቀሪዎቹም በቅርቡ ሙሉ በሙሉ ወደ ስራ ይገባሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል።
በሌላ በኩል፣ የአማራ ክልል የሲቪል ማኅበራት ሕብረት ዋና ዳይሬክተር አቶ ንጋቱ ደስታ የመራጮች ትምህርት እንዳይሰሩ የተለያዩ ተግዳሮቶች እንደገጠሟቸው ተናግረዋል።
“ሕብረቱ በምርጫ ቦርድ መመሪያ መሠረት እየሠራ ቢሆንም፣ የፋይናንስ እጥረት እና በአንዳንድ አካባቢዎች ባለው የጸጥታ ስጋት መራጮችን የማስተማር ስራውን በሁሉም የክልሉ አካባቢዎች ተደራሽ ለማድረግ እንቅፋት ፈጥሯል” ሲሉ አብራርተዋል።
ምክር ቤቱ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት ሂደቱ ሰላማዊ እንዲሆንና የዜጎች የመምረጥ መብት እንዲረጋገጥ የማድረግ ተግባሩን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አጽንኦት ሰጥተውበታል።
