የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከ200 ሺህ ብር በታች ካፒታል ያላቸውን ነጋዴዎች በኢ-መደበኛ የንግድ ሥርዓት ውስጥ እንደሚካተቱ አስታወቀ።
ይህን ይፋ ያደረጉት የከተማ አስተዳደሩ ንግድ ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሃቢባ ሙሃመድ እንደገለጹት፣ መደበኛ ባልሆነ የንግድ ሥርዓት ውስጥ የሚካተቱ ነጋዴዎች ቋሚ የሥራ ቦታ የሌላቸው፣ በየዓመቱ የሚታደስ የንግድ ፈቃድ የሚያገኙ እንዲሁም በግብር ሥርዓት ውስጥ ያልተካተቱ መሆናቸውን አስረድተዋል።
ከዚህ ቀደም በ 2009 በነበረው አዋጅ ከ10 ሺህ ብር በታች ካፒታል ያላቸው ነጋዴዎች ኢ-መደበኛ ተብለው እንደነበር አስታውሰው፣ በተሻሻለው አዋጅ ግን ይህ መጠን ወደ 200 ሺህ ብር ከፍ ብሏል ብለዋል።
በተጨማሪም ከዚህ በፊት በኢ-መደበኛ የንግድ ሥርዓት ውስጥ ለሚንቀሳቀሱ ነጋዴዎች የጊዜ ገደብ እንዳልነበረ የጠቆሙት ኃላፊዋ፣ በአዲሱ አዋጅ መሰረት በተሰጣቸው የሥራ ቦታ ላይ ለሁለት ዓመት ብቻ እንዲሠሩ የሚፈቀድላቸው ሲሆን፣ ካፒታላቸው 200 ሺህ ብር ሲደርስ ወደ መደበኛ የንግድ ሥርዓት እንደሚካተቱ አብራርተዋል።
ወይዘሮ ሃቢባ መደበኛ ያልሆነ የንግድ ሥርዓት በሁለት እንደሚከፈልም ገልጸዋል። እነዚህም ቋሚ በሆነ ቦታ ላይ የሚሠሩ እና በጎዳናዎች ላይ የሚንቀሳቀሱ ናቸው። በጎዳናዎች ላይ የሚሠሩት ነጋዴዎች በተወሰነ ቀን እና የሥራ ሰዓት ብቻ የንግድ ሥራቸውን እንዲያከናውኑ እንደሚደረግም አክለዋል።
